ኢትዮጵያ ቡና ዕሁድ ከአሰልጣኝ ውበቱ አባተው ክለብ ጋር የወዳጅነት ጨዋታን ያደርጋል።
ኢትዮጵያ ቡና የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ የፊታችን ቅዳሜ በ20ኛው ሳምንት መርሀግብሩ ሲመለስ ከቅዱስ ጊዮርጊስ ጋር የሚገናኝ ቢሆንም ጨዋታው ወደ ሌላ ጊዜ በመዛወሩ ምክንያት የወዳጅነት ጨዋታን የፊታችን ዕሁድ የካቲት 15 በአዲስ አበባ ስታዲየም ለማድረግ ማሰቡ ተሰምቷል።
ቡናማዎቹ የምስረታቸውን 50ኛ አመት በማስመልከት በሚያደርጉት የወዳጅነት ጨዋታ በኢትዮጵያዊ አሰልጣኝ ውበቱ አባተ የሚሰለጥነውን ጃሙስ ክለብን እንደሚገጥሙ የታወቀ ሲሆን የክለቡም 47 የልዑካን አባላት ነገ አዲስ አበባ ይገባሉ።
በነገው ዕለት ወደ ኢትዮጵያ እንደሚመጣ የሚጠበቀው የደቡብ ሱዳኑ ክለብም ከአራት ወራት በፊት ኢትዮጵያ መጥቶ በሀዋሳ ከተማ ዝግጅት ካደረገ በኋላ ይህ ለሁለተኛ ጊዜ ነው ወደ ሀገራችን ሲመጣ።


