ታሪክን ሰንዶ ገደል አፋፍ ለቆመው ቅዱስ ጊዮርጊስ እግር ኳስ ክለብ ለበሽታው መድሀኒትን ወይስ የከፋ በሽታ …? በሚል ዘርዘር ባለ መልኩ ይህንን ሀሳብ እንካቹ ብለናል !
በኢትዮጵያ ውስጥ እግር ኳስን በብዙሀኑ ልብ ውስጥ ታትሞ እንዲቀር ከነጮች ጋር ትግል ውስጥ በመግባት ሀገሪቷ ላይ ተወዳጅ ስፖርት ሆኖ ዛሬም ድረስ እንዲቀር የቅዱስ ጊዮርጊስን ያክል ሚና ያለው ክለብም ሆነ የሚስተካከለው የለም ፣ የኢትዮጵያን የእግር ኳስ ታሪኮቿን ላገላበጠ ከፊት ራሱን ያሰፈረው ይህ ዘመን ተሻጋሪው ክለብ እንደሆነ ማንም የማንንም ምስክር ሳያሻ ታሪኩን እና ስኬቱን የተመለከተ ሁሉ በቀላሉ መረዳት ይችላል።
የቅዱስ ጊዮርጊስን መለያ ላለፉት እልፍ አመታት የለበሱ አስልጣኞች እና ተጫዋቾች በተለያዩ አጋጣሚዎች ክለቡ የአሸናፊነት ምልክት እና የድል መሠረት እንደሆነ ደጋግመው ሲናገሩ የሚደመጥ ሲሆን ይህንንም ንግግር ለማረጋገጥ ቡድኑ ያገኛቸውን ለቁጥር የሚያዳግቱ ዋንጫዎችን አስተውሎ ምን ያህል እልፍ የድል ጥጋቦችን እንደሸመተ በክለቡ ውስጥ ላሉም ሆነ ለነበሩትም ብቻ ሳይሆን እንዲሁ ለተመለከቱ እና ታሪኩንም ለሰሙ በሙሉ ልብን የሚያሞቅ የደስታ ሲቃ ብቻ ባለቤት መሆን እንደቻለ ማረጋገጥ ይቻላል። ቅዱስ ጊዮርጊስ በርካታ ተጫዋቾችን አፍርቷል ለራሱ ብቻም ሳይሆን ለሀገርም ጭምር እንካቹ ብሎ ለግሷል ፣ በተለያዩ ክለቦች የሚጫወቱ ተጫዋቾችም የክለቡን መለያ ለመልበስ ትልቁ ህልማቸው እንደሆነ በተደጋጋሚ ሲያነሩ የሚሰማ ሲሆን በለስ ቀንቷቸው ቡድኑን የሚቀላቀሉትም በገንዘብ ሆነ በስም ከፍ ያለውን ቦታ ሲያገኙ ህይወታቸውም የተቃና መንገድን ሲሻ ይስተዋልም ጭምር ነበር።
ቅዱስ ጊዮርጊስ ከአመታት በፊት በገንዘብም ይሁን በትልልቅ ስፖንሰሮች በመደገፍ ከሀገራችን እግር ኳስ ክለቦች የገዘፈ ስም የነበረው ሲሆን ክለቡ በሀብት በተንበሸበሸበት በእነዛ አመታት እንደ ክለብ ቡድኑ ራሱን እንዲችል ክለቡን ይመሩ የነበሩ አመራሮችም ይሁኑ ግለሰቦች እንዳላቸው ሀብት መዋለ ንዋይ መሠረተ ልማት ፣ የገበያ አዳራሾች ፣ ህንፃዎች ፣ ሆቴሎች እና መጠነኛ ሜዳዎች እና ዘመናዊ ስታዲየሞችን ገንብተው ክለብ እፎይ እንዲል ማድረግ ሲጠበቅባቸው ገንዘብ አለ ሌላ ወጪን እንቢ በሚል አጉል ብሂል ከኪስ ማውጣትን እንጂ ክለቡ ነገ ምን ያስፈልገዋል ? እንዳይቸገርስ የራሴ የሚለውስ ምን ሊኖረው ይገባል ? የሚል አስተሳሰብን በዕቅዳቸው ማካተት ሳይችሉ በመቅረታቸው ክለቡ አሁን ላይ ላለበት ፈታኝ ቁመና ላይ እንዲገኝ ዳርጎታል።
- ማሰታውቂያ -
እንደ ሀገር ስሙ በማይፋቅ መዝገብ ላይ ተፅፎ ለዘመናት ተጫዋቾች የቅዱስ ጊዮርጊስን መለያ ለመልበስ የሚናፍቁለት ያ ስመ ገናናው ክለብ በግለሰቦች የግል ንትርክ እና ራስ ወዳድነት ብዙሀኑ የእኔ የሚለው የህፃኑም ፣ የወጣቱም ፣ የአዛውንቱም የሆነው ክለብ ዛሬ ግን ስሙን ብቻ ይዞ በብዙ ፈተናዎች ውስጥ መጓዙን ቀጥሏል። ያ ከፍ ባለ ገንዘብ ብቻ ስፖንሰር ፈላጊ የነበረው ግለሰቦችም ባላቸው ጊዜ ለክለቡ የሀብት ምንጭ መፍጠር ያልቻሉለት በአንድ ወቅትም ከኢትዮጵያም አልፎ በአፍሪካ አህጉር ከሚጠሩ ትልልቅ ክለቦች መካከል ስሙ በጉልህ የሰፈረው ፈረሰኛ አሁን ደመወዝ መክፈል አቅቶት ፣ ክለቡን ከፍ በማያደርግ ትንንሽ ስፖንሰሮች መዳፍ ስር ለመውደቅ ተገዷል።
ብዙሀኑ የቆሰሉለት አለፍ ሲልም የሞቱለትን ክለብ ለማዳን ከግለሰቦች አስተሳሰብ በመውጣት ሁሉም የክለቡ ወዳጅ በሚጠቅመው ፣ ክለቡም በገንዘብ ራሱን ቀና ወደሚያደርግበት መንገድ እንዲመጣ እሹሩሩ ሳይሆን ተግባር ላይ ብቻ ሊያተኩር ብቻ እና ብቻ ያስፈልጋል እና ታሪክን ሰንዶ ገደል አፋፍ ለቆመው ክለብ ለበሽታው መድሀኒትን እንጂ የከፋ በሽታ አያስፈልገውም እና ሁሉም የድርሻውን ሊወጣ ግድ ይላል።


