በኢትዮጵያ እግር ኳስ ታሪክ ውስጥ ስመ ጥሩ ክለብ አሁንም በሁለት ተጨማሪ ተጫዋቾች በፊፋ ክስ ቀረረበት።
ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ ከፋይናንስ ጉዳዮች ጋር በተያያዘ በድግግሞሽ ስሙ እየተነሳ የሚገኘው ቅዱስ ጊዮርጊስ ከቀናቶች በፊት በጋናዊው አማካይ ክዋሜ ፍሪምፓንግ አማካኝነት በፊፋ በኩል ክስ ቀርቦበት ክለቡ ለተጫዋቾች የጠየቀውን ጥቅማጥቅም ተፈፃሚ እንዲሆን በሚል በፊፋ ዳጎስ ያለ የገንዘብ ክፈል እና በዝውውርም ክለቡ እንዳይካፈል ዕገዳ መጣሉ የሚታወስ ሲሆን አሁን ደግሞ ሁለት የውጪ ዜጎች ለፊፋ አቤት ብለዋል። በአሁኑ ሰዓት ክለብ አልባ የሆኑት የታንዛኒያውን ክለብ ያንጋ አፍሪካን ለቆ ቅዱስ ጊዮርጊስን ተቀላቅሎ የነበረው አማካዩ ጊፍት ፍሬድ እና አይቮሪኮስታዊው አጥቂ መሐመድ ኮኔ ለፊፋ ያልተከፈለን በድምሩ ከአስራ አምስት ሚሊዮን ብር በላይ አለን ይከፈለን በሚል ያቀረቡት ክስ ፊፋ ተቀብሎ ለኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌድሬሽን እና ለክለቡ በኢሜል አሳውቋል።
ክለቡ የማይከፍል ከሆነ በየቀኑ ታሳቢ በሚደረግ ወለድ እጥፍ ቅጣት ሊጠብቀው እንደሚችል ያገኘውት መረጃ አመላክቷል። ከቅዱስ ጊዮርጊስ ባሻገር አዳማ ከተማ የዛሬ ሦስት አመት ለሦስት የውጪ ዜጋ ተጫዋቾች ያልከፈለው ገንዘብ እንዳለ ክለቡም በዝውውር አይካፈልም ተብሎ ከወራት በፊት ዕገዳ በፊፋ ቢጣልበትም ክለቡ ግን በዝውውር መሳተፉ አስገራሚ የነበረ ሲሆን አሁንም በተመሳሳይ ሌላ ደብዳቤ የደረሰው ክለብ ሆኗል። በአንድ ወቅት የፕሪምየር ሊጉ ተካፋይ ክለብ የሆኑት ወልቂጤ እና ጅማ አባጅፋርም ደብዳቤ የተላከላቸው ሌሎቹ ክለቦች ቢሆኑም ፌድሬሽኑ ግን በየአመቱ የማስፈፀም ውስንነት እያሳየ መቀጠሉም ብዙሀኑን አስገርሟል።


