ሲዳማ ቡና ወሳኝ ድል ሲጎናፀፍ ሸገር ከተማ እና ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ 1ለ1 በሆነ አቻ ውጤት አጠናቀዋል።
ሸገር ከተማ 1-1 ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ
ወንበራቸው መነቃነቅ የጀመረው አሰልጣኝ አሸናፊ በቀለ በመጀመሪያዎቹ ሀያ ደቂቃዎች ውስጥ ቡድናቸው የወሰደውን የእንቅስቃሴ ብልጫ ተከትሎ ከመስመር በሚነሱ ኳሶች በመጫወት ጎል ያስቆጠሩት በአጋማሹ አካፋይ ሰዓት ላይ ነበር። ከቀኝ ሔኖክ አሻምቶ ፍቅሩ አለማየሁ በግንባር ገጭቶ ለጥቂት ካመለጥችው አጋጣሚ በኋላ 20ኛው ደቂቃ ላይ ዘነበ ከድር የግል ጥረቱን ተጠቅሞ ከግራ ያሻገረውን ኳስ በሴካፋ ከ17 አመት በታች ዋንጫ የውድድሩ ከፍተኛ ጎል አስቆጣሪው እና ለመጀመሪያ ጊዜ ቋሚ ሆኖ የገባው ወጣቱ ዳዊት ካሳው የመጀመሪያ የሊግ ጎሉን ከመረብ አዋህዶ ቡድኑን ቀዳሚ አድርጓል።
ፈጣን አጥቂዎቻቸውን በመጠቀም አቻ ለመሆን ጥረት ያደረጉት ንግድ ባንኮች 30ኛው ደቂቃ ላይ ከራሱ የግብ ክልል በረጅሙ የተላከውን ኳስ ሳይመን ፒተር ለማግኘት ጥረት ሲያደርግ ባልተመጣጠነ ሀይል በገዛኸኝ ከተማ እና ዘነበ ከድር ሳጥን ውስጥ በመገፍተሩ የተሰጠውን የፍፁም ቅጣት ምት አዲስ ግደይ ወደ ጎልነት ለውጦ የውድድር ዘመኑን ሰባተኛ ጎል አስቆጥሯል።
- ማሰታውቂያ -
ከዕረፍት መልስ ሸገሮች አሸንፈው ለመውጣት በተለይ ኮሪደሩን በይበልጥ ለመጠቀም ጥረት ቢያደርጉም ጥንቃቄን መርጠው በተወሰነ መልኩ መልሶ ማጥቃትን የተጠቀሙትን የንግድ ባንክ የኋላ ክፍል ማስከፈት ተስኗቸው ጨዋታው በመጨረሻም 1ለ1 ተጠናቋል።
ሲዳማ ቡና 2-0 ሀድያ ሆሳዕና
እጅግ ከፍ ባለ የማጥቃት ደመ ነብስ መንቀሳቀስን በጊዜ የጀመሩት ሲዳማ ቡናዎች ደቂቃው ብዙም ሳይሄድ የመሪነት ጎላቸውን አግኝተዋል። 2ኛው ደቂቃ ላይ በጥሩ ቅብብል የመጨረሻው ሜዳ ላይ ሀብታሙ ታደሠ ያቀበለውን ኳስ የሀድያ ሆሳዕና ተከላካዮች ስህተት ታክሎበት ቡድኑ ቀዳሚ አድርጓል። ሲዳማ ቡናዎች ለተጨማሪ ጎል ጫና መፍጠራቸውን ቀጥለው አጋማሹ ሊገባደድ በተሰጠው ጭማሪ ላይ 90+4 ደቂቃ ላይ ዮሴፍ ዮሐንስ የተጋጣሚ ቡድን ተጫዋች በተሳሳተ አቅጣጫ ያቀበለው በግምት ከሰላሳ ሜትር ርቀት ከሳጥን ውጪ በማስቆጠር የቡድኑን የጎል መጠን አስተማማኝ አድርጓል።
በሁለተኛው አጋማሽ ጨዋታው ተመልሶ ቢቀጥልም እምብዛም የተሳኩ ሙከራዎች ሳንመለከት ጨዋታ በመጀመሪያው አጋማሽ ጎሎች በሲዳማ ቡና 2ለ0 አሸናፊነት ሲጠናቀቅ ክለቡም የሊጉን መሪነት አጠናክሮ ቀጥሏል።
ትላንት ቅዱስ ጊዮርጊስ ከ ወላይታ ድቻ 1ለ1 አርባምንጭ ከተማ ከሀዋሳ ከተማ ጋር ደግሞ ያለ ጎል መፈፀማቸው ይታወሳል።


