ቅዱስ ጊዮርጊስ ስፖርት ማህበር ከቲና ማርት የኤሌክትሮኒክስ ገበያ ጋር የስራ ስምምነት ተፈራርሟል።
ስምምነቱን የቲና ማርት ስራ አስኪያጅ አቶ ኢዘዲን ካሚል እና የቅዱስ ጊዮርጊስ ስፖርት ክለብ ዋና ስራ አስኪያጅ ዶ/ር ፍፁም ካሳዬ ፈርመዋል። በስምምነቱ መሰረት ቅዱስ ጊዮርጊስ በቲና ማርት የኤሌክትሮኒክስ ገበያ በኩል በበይነ መረብ ምርቶቹን በዋነኝነትም ማልያዎችን የሚሸጥ ይሆናል። የሚቀርቡት ምርቶች ላይም 7% ጭማሪ ተደርጎባቸው በቲና ማርት በኩል እንደሚቀርቡም በስምምነቱ ወቅት ተመላክቷል። በሁለቱ ተቋማት መካከል የተደረገው ስምምነት ለአንድ ዓመት የሚቆይ ስለመሆኑም ተገልጿል።
ቲና ማርት የጨዋታ ቀናት ላይን ጨምሮ የተለያዩ መርሐግብሮችን ለማዘጋጀት 10 ሚልዮን ብር መመደቡን የተገለፀ ሲሆን በሲስተሙ የክለቡ የአባልነት መመዝገቢያ መንገድም ተመቻችቷል ተብሏል። በተጨማሪም ክለቡን ለማገዝ ለሚፈልጉ ደጋፊዎች ከየትኛውም የዓለም ክፍል ሆነው ድጋፍ ማድረግ የሚችሉበት መንገድ መዘርጋቱም ተገልጿል። ቲና ማርት ለሽያጭ የሚቀርቡትን ማልያዎች ከክለቡ እንደተረከብ ወድያውኑ ሽያጩን እንንደሚጀምር ተነግሯል። ቲና ማርት ከአስር የሀገር ውስጥ የክፍያ አማራጮች በጋራ በመስራት ላይ የሚገኝ ሲሆን ተጠቃሚዎች በነዚህ አማራጮች ክፍያቸውን በመፈፀም ግብይቱ መፈፀም ይችላሉ።



