በትናንትናው ዕለት በተደረገው እና ያለ ግብ በተጠናቀቀው የሸገር ደርቢ ጨዋታ ላይ ኢንተርናሽናል ዋና ዳኛ ቴዎድሮስ ምትኩ ያሳለፏቸው ጥቂት የማይባሉ ውሳኔዎች አነጋጋሪ ሆነው ቀጥለዋል።
በተለይም በተገኑ ተሾመ ፣ አብዱልሀፊዝ ቶፊቅ እና ፍፁም ጥላሁን ላይ በፍፁም ቅጣት ምት ሳጥን ውስጥ የተሰሩ ጥፋቶችን በዝምታ ማለፋቸው በተለይም በርካታ የቅዱስ ጊዮርጊስ ክለብ አባላት እና ደጋፊዎችን አስቆጥቷል።
ክለቡ ቅዱስ ጊዮርጊስም ከደቂቃዎች በፊት በይፋዊ የማህበራዊ ትስሰር ገፆቹ ይፋ ባደረገው መረጃ መሰረት በጨዋታው ላይ የዳኝነት በደል ደርሶብኛል በማለት ለኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን እና ለኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ አክስዮን ማህበር አቤቱታውን አቅርቧል።
ክለቡ በአቤቱታውም ጉዳዩ ሊመረመር እና የማያዳግም እርምጃ ሊወሰድበት የሚገባ ነው ሲል ገልጿል።
- ማሰታውቂያ -
ቅዱስ ጊዮርጊስ ያስገባው ሙሉ አቤቱታ እንደሚከተለው ቀርቧል።
“በየዘመኑ ተደጋጋሚ የሆኑ የዳኝነት በደሎች ቢፈፀሙብንም በሂደት ይስተካከላሉ በሚል እምነት በትዕግስት አሳልፈናል፡፡
ዳኛ ገለልተኛ ምስከርና የውድድር መሪ ነው፤ በዚህም የተነሳ የተለየ መብት አለው፡፡ ስህተት እንኳን ቢሠራም ውሳኔው የመጨረሻና የማይገሰስ ነው። ነገር ግን የእርሱ የተለዩ መብቶች ተጠያቂነትን ማምጣት አለባቸው:: አሁን አሁን በስታዲየም የሚፈፀሙ ግልጽና አድሏዊ የሆኑ የዳኝነት በደሎች ተጫዋቾችና የቡድን አባላት እንዲሁም ተመልካቹ ህዝብ የሥነ ምግባር ጥሰት ውስጥ እንዲገባ የሚገፋፉ ሆነው ታይተዋል፡፡
ጥር 25 ቀን 2017 ዓ.ም በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ሜዳ በእኛና በኢትዮጵያ ቡና መካከል የተደረገውን ጨዋታ በመሐል ዳኝነት የመሩት ኢንተርሽናል ዳኛ ቴዎድሮስ ምትኩ ሦስት የፍፁም ቅጣት ምቶችን የከለከሉበት ሁኔታ አግራሞት የፈጠረ ቢሆንም ጉዳዩ መመርመር የሚያስፈልገውና የማያዳግም እርምጃ ሊወሰድበት የሚገባ፣ ለእግር ኳሱ እድገት ፀር የሆነ አካሄድ ነው፡፡ ሦስቱንም የቪዲዮ ምስሎች በአጽንዖት እንድትመለከቱት እያይዘን አቅርበናል፡፡ ባለፈው ዓመት የውድድር ዘመን እኚሁ ዳኛ የፈፀሙበንን በደል በቪዲዮ አስደግፈን ማቅረባችን የማይዘነጋ ነው:: ሆኖም ከሚመለከተው አካል ለአቤቱታችን መልስም ሆነ ጉዳዩን አስመልከቶ የተወሰደ አንዳችም የእርምት ርምጃ ስለመወሰዱ የተገለፀ ነገር ባለመኖሩ ይኸው ዘንድሮም ጥፋቶቹ ተጠናከረውና ተበራከተው ቀጥለዋል።
በቀጣይም ትኩረት በሚሹ ወሳኝ ጨዋታዎች ላይ ጥንቃቄ ካልተደረገ በስተቀር የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ውድድር በዳኝነት በደሎች የተነሳ ከፍተኛ ውዝግብ ውስጥ ሊገባ እንደሚችል መገመት እያዳግትም። ስለሆነም የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽንም ሆነ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ አ.ማ. በብርቱ ሊያሰቡበት የሚገባና አስቸኳይ ትምህርት ሰጪ ርምጃዎችን በመውሰድ ሁኔታዎችን መቆጣጠር አስፈላጊ መሆኑን ማስገንዘብ እንወዳለን።”


