የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 18ኛ ሳምንት የሶስተኛ ቀን ጨዋታዎች በዛሬው ዕለት ሲደረጉ ከአመሻሽ 12:00 ጀምሮ የተደረገው የአርባምንጭ ከተማ እና ሀድያ ሆሳዕና ጨዋታ 3 – 3 ተጠናቋል።
በጨዋታው ሀድያ ሆሳዕናዎቹ ገና በጊዜ 2 – 0 መሪ መሆን ነበር።
በ4ኛው ደቂቃ ላይ ሄኖክ አርፊጮ ከቅጣት ምት በቀጥታ ወደ ግብ የመታው ኳስ በቀጥታ የሀድያ ሆሳዕና መረብ ላይ አርፏል።
በ14ኛው ደቂቃ ደግሞ ዳግም ንጉሴ ከማዕዘን የተሻገረለትን ኳስ በግንባሩ ገጭቶ በማስቆጠር የከቤራዎቹን መሪነት ወደ 2 – 0 ከፍ አድርጓል።
- ማሰታውቂያ -

በ26ኛው ደቂቃ ላይ ዳግም ንጉሴ በአህብዋ ብሪያን ላይ በሳጥን ውስጥ የሰራውን ጥፋት ተከትሎ አዞዎቹ የፍፁም ቅጣት ምት ቢያገኙም ጥፋቱ የተሰራበት ብሪያን ሳይጠቀምበት ቀርቷል።
የመጀመሪያው አጋማሽ ሊጠናቀቅ በተቃረበበት ወቅት ግን አዞዎቹ ወደ ጨዋታው የመለሳቸውን ግብ ከመረብ አሳርፈዋል።
በ45+3 ደቂቃ ላይ ከአርባምንጭ የቀኝ አቅጣጫ ወደ ሳጥኑ የተሻገረውን ኳስ ቡታቃ ሸመና በደረቱ አረጋግቶ የሀድያ ሆሳዕናውን ግብ ጠባቂ ያሬድ በቀለ ስህተትም ታክሎበት ግቡን አስቆጥሯል።
በርካታ ክስተቶችን እያስመለከተ በቀጠለው ጨዋታ በሁለተኛው አጋማሽም ተጨማሪ ግቦችን አክሏል።
በ60ኛው ደቂቃ ላይ የፍፁም ቅጣት ምቱን መጠቀም ያልቻለው አህባዋ ብሪያን በረጅም የተላከለትን ኳስ የያሬድ በቀለን ሁለተኛ የጊዜ አጠባበቅ ስህተት ተጠቅሞ አርባምንጭ ከተማን አቻ አድርጓል።
ከግቡ መቆጠር ጥቂት ደቂቃዎች በኋላ ግን አዞዎቹ አንድ ተጫዋች በቀይ ካርድ ማጣታቸውን ተከትሎ ቀሪውን ደቂቃ በ10 ተጫዋቾች ለመጨረስ ተገደዋል።
ተከላካዩ አሸናፊ ፊዳ ከኳስ ውጪ በሆነ እንቅስቃሴ እዮብ አለማየሁ ላይ የመታው ሲሆን በቅርበት ሆነው ሁነቱን የተመለከቱት የዕለቱ ዋና ዳኛ በቀጥታ የቀይ ካርድ ከሜዳ አስወግደውታል።
ጨዋታው 75ኛ ደቂቃ ላይ በደረሰበት ወቅት ግኑ አርባምንጭ ከተማዎች 2 – 0 ሲመሩበት የነበረውን የጨዋታ ውጤት ወደ 3 – 2 መቀየር የቻሉበትን ግብ አስቆጥረዋል።
ይሁን እንደሻው ከቆመ ኳስ ወደ ግብ ክልል ያሻገረውን ኳስ ቡታቃ ሸመና በጭንቅላት ገጭቶ በማስቆጠር የአዞዎቹን ደጋፊዎች አስፈንድቋል።
ጨዋታው በአርባምንጭ ከተማ አሸናፊነት የተጠናቀቀ በመሰለበት የመጨረሻ ደቂቃዎች ላይ ግን ጫና ፈጥረው የነበሩት ከቤራዎቹ 3 – 3 የሆኑበትን ግብ በብሩክ ማርቆስ አማካይነት አግኝተዋል።
በመጨረሻም ጥሩ ፉክክር እና በርካታ ክስተቶች የነበረው ጨዋታ በሶስት አቻ ውጤት የተጠናቀቀ ሲሆን ውጤቱንም ተከትሎ ሀድያ ሆሳዕና ነጥቡን 27 ሲያደርስ አርባምንጭ ከተማ በበኩሉ ነጥቡን 24 አድርሷል።
በ19ኛው ሳምንት ጨዋታዎች ሀድያ ሆሳዕና ከቅዱስ ጊዮርጊስ አርባምንጭ ከተማ ደግሞ ከኢትዮ ኤሌክትሪክ ይገናኛሉ።
በዕለቱ በቀዳሚነት በተደረገው ጨዋታ ወላይታ ድቻ መቀሌ 70 እንደርታን አሸንፏል።
እምብዛም ሳቢ ባልነበረው ጨዋታ ካርሎስ ዳምጠው በ73ኛው ደቂቃ ላይ ያስቆጠረው ግብ ለጦና ንቦቹ ሶስት ነጥብ ማሳካት በቂ ነበረ።
ካርሎስ ዛሬ ያስቆጠረውን ግብ ተከትሎም በውድድር ዓመቱ በሊጉ ያስቆጠራቸውን የግብ ብዛቶች 4 ማድረስ ችሏል።
ድሉ ለወላይታ ድቻ ከተከታታይ ሶስት ድል አልባ እና ሁለት ተከታታይ ሽንፈቶች በኋላ የተገኘ ሲሆን መቀሌ 70 እንደርታ በበኩሉ ሊጉ አዳማ ላይ መካሄድ ከጀመረ በኋላ የመጀመሪያ ሽንፈቱን አስተናግዷል።
በቀጣይ ሳምንት መርሐግብር ወላይታ ድቻ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሲጫወት መቀሌ 70 እንደርታ አራፊ ቡድን ነው።


