የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ በብሔራዊ ቡድን ጨዋታዎች ምክንያት ከተቋረጠ በኋላ በመጪው ቅዳሜ በአራተኛ ሳምንት ጨዋታዎች ይመለሳል።
በሳምንቱ ከሚደረጉት ጨዋታዎች መካከል ዕሁድ የሚደረገው የቅዱስ ጊዮርጊስ እና ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጨዋታ ተጠባቂ ነው።
ቢሾፍቱ በሚገኘው የይድነቃቸው ተሰማ አካዳሚ ልምምዱን በማድረግ ላይ የሚገኘው የቅዱስ ጊዮርጊስ ክለብ ዋና አሰልጣኝ የሆኑት አሰልጣኝ ፋሲል ተካልኝ ከክለቡ የሬድዮ ፕሮግራም ጋር ስለነበራቸው የዝግጅት ጊዜ እና ተያያዥ ጉዳዮች ሀሳባቸውን ሰጥተዋል።
“የተወሰነ እረፍት ከወሰድን በኋላ አዳዲስ ተጫዋቾች ከቡድኑ ጋር የማዋሀድ እና ባለፉት ጨዋታዎች ላይ የታዩ ደካማ ጎኖች የማሻሻል ፤ በአካልም በአዕምሮ ተጫዋቾች የማዘጋጀት ስራዎች ሰርተናል” ሲሉ አሰልጣኝ ፋሲል ተካልኝ ተናግረዋል።
- ማሰታውቂያ -
አሰልጣኙ የቡድናቸውን አቅም ከፍ ያደርጋሉ ብለው ስለሚያስቧቸው እና ከውጪ ሀገራት ስለፈረሙት ተጫዋቾች መረጃ ሲሰጡም ፤ የኮትዲቯራዊው አጥቂ መሀመድ ኮኔ የወረቀት ስራዎች አለመጠናቀቁን ገልፀዋል።
“አንደኛው አጥቂያችን ኮኔ ዘግይቶ ቢሆንም የገባው ሶስቱም ተጫዋቾች በነበረው የእረፍት ጊዜ ከኛ ጋር ዝግጅታቸውን አድርገዋል።ከቡድኑ ጋር ለማዋሀድ እየሞከርን ነው። ኮኔ ከመኖሪያ ፈቃድ ጋር በተያያዘ አስተዳደራዊ ጉዳዩ አላለቀም። ምናልባት በዚህ ሁለት ቀናት ውስጥ ተጠናቆ ከኛ ጋር ወደ ድሬዳዋ እንደሚያመራ እጠብቃለሁ።”
ቅዱስ ጊዮርጊስ በሊጉ ካደረጋቸው ሶስት ጨዋታዎች ወልዋሎ አዲግራትን ሲያሸንፍ በፋሲል ከነማ እና መቀሌ 70 እንደርታ ሽንፈቶችን አስተናግዷል። አሰልጣኝ ፋሲል የተጫዋቾቻቸው ስነ ልቦና ላይ ክፍተቶች መኖራቸውን በማንሳት ይህንን ለማስተካከልም ጠንካራ ስራዎች በመስራት ላይ እንደሚገኙም ጠቁመዋል።
“ተጫዋቾችን በየጊዜው በአካል ብቃትም በአዕምሮም ለማዘጋጀት እንጥራለን። ወጣቶች ከመሆናቸው ጋር ተያይዞ የሚገጥሙንን ችግሮች በንግግር እና በስራ ለመፍታት እየሞከርን ነው።”
“አንዳንድ ጊዜ በሜዳ ላይ ያሰብነው ነገር ሳይሳካ ሲቀር በቀላሉ የመሰበር የመደንገጥ ነገር በተጫዋቾቻችን ላይ አለ። ይሄ እንግዲህ ከቅዱስ ጊዮርጊስ ታላቅነት እና ካለው ሀላፊነት ጋር ተያይዞ እሱን የመሸከም አቅም ነው።እንግዲህ በሂደት ይቀረፋል ብለን እናስባለን። ከዚህ ውጪ ተጫዋቾቹ ለመስራት ለማሸነፍ የሚጠበቅባቸውን ለማድረግ ያላቸው ጉጉት ከፍተኛ ነው።”
ቡድኑ በሶስተኛው ሳምንት ከመቀሌ 70 እንደርታ ጨዋታ ያደረጉበት ሰዓት ላይ ቅሬታ እንዳላቸው ያነሱት አሰልጣኙ ጉዳዩን አስቀደምውም ለሚመለከተው አካል በማሳወቅ መጠየቃቸውን ገልፀዋል።
“ከመቀሌ ጋር ስንጫወት የፊፋን እና የሊግ አክስዮን ማህበሩን ህግ የሚጋጭ ነው። አንድ ቡድን ከ72 ሰአታት በኋላ ነው መጫወት ያለበት ይላል ህጉ እኛ ደግሞ ስንጫወት 69 ሰዓት ነው።”
ከጨዋታዉ አስቀድሞ ቀርበው መጠየቃቸውን እና ማስረዳታቸውን ያነሱት አሰልጣኝ ፋሲል በነበረው ጠባብ ጊዜ ጨዋታውን ማድረጋቸው ለሽንፈቱ ዋነኛ ምክንያት እሱ ነው ባይባልም ተፅዕኖ ግን አልነበረውም ማለት አይቻልም ብለዋል።
ከመቼውም ጊዜ የበለጠ የክለቡ አባላቶች ደጋፊውን ይፈልጋሉ ያሉት አሰልጣኝ ፋሲል ደጋፊው በቀጣይ ጨዋታዎች ላይ ቡድኑን እንዲያበረታታ ጥሪ አቅርበዋል።
በቀጣይ ሶስት ጨዋታዎች ላይ ከአራት እስከ አምስት ቀናት ልዩነቶች አሉ ስለዚህ እነዚህን ሶስት ጨዋታዎች እየተመላለስን ነው የምንጫወተው።
አርብ ልምምዳችንን ከሰራን በኋላ ቅዳሜ ወደ ድሬዳዋ በማቅናት በጨዋታው ማግስት ሰኞ እንመለሳለንም ብለዋል።
ቅዱስ ጊዮርጊስ በሊጉ አራተኛ ሳምንት መርሐግብር በመጪው ዕሁድ ምሽት 1:00 ጀምሮ በድሬዳዋ ስታድየም ጨዋታውን ያደርጋል።


