ከኢንስትራክተር አብርሃም መብራቱ ጋር ከተለያዩ በኋላ አሰልጣኝ ዘላለም ሽፈራሁን(ሞሪንሆ) በዋና አሰልጣኝነት የቀጠሩት ሰበታዎቻ አሁን ደግሞ እጅግ ዘግይተው ወደ ዝዉዉሩ በመግባት ሶስት አዳዲስ ተጫዋቾችን ወደ ቡድናቸዉ መቀላቀል ችለዋል።
የቀድሞዉ አርባምንጭ ከተማ፣ ሀላባ ከተማ ፣ድሬዳዋ ከተማ እና አክሱም ከተማ ተጫዋች የነበረዉ ዘካርያስ ፍቅሬ በተጠናቀቀው የዉድድር አመት ወደ መከላከያ አምርቶ በከፍተኛ ሊጉ መጫዎቱ የሚታወስ ሲሆን ፤ መከላከያ ከከፍተኛ ሊጉ ወደ ቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ እንዲያድግ ትልቅ ድርሻ የነበረዉ ተጫዋቹ በቀጣዩ የዉድድር አመት ደግሞ ለሰበታ ከተማ ለመጫወት የሁለት አመት የስምምነት ዉል ፈርሟል።
ሁለተኛዉ ፈራሚ ደግሞ በ2012 የዉድድር አመት መከላከያን የተቀላቀለዉ እና ዘንድሮ ክለቡ መከላከያ ከከፍተኛ ሊጉ ወደ ቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ሲያድግ የስብስቡ አካል የነበረዉ አጥቂዉ መሀመድ አበራ ለሁለት አመታት ከቆየበት መከላከያ በመልቀቅ ወደ ሰበታ ከተማ ማምራት ተረጋግጧል።
ሶስተኛ ፈራሚ ሆኖ ክለቡን የተቀላቀለዉ ደግሞ ተከላካዩ በረከት ሳሙኤል ሲሆን በድሬዳዋ ከተማ ረዘም ላሉ ዓመታት ሲጫዎት የምናዉቀዉ ተከላካዩ ረጅም አመታትን ካሳለፈበት ድሬዳዋ ከተማ በመልቀቅ የአሰልጣኝ ዘላለም ሽፈራዉን ሰበታ ከተማ በሶስት አመት የኮንትራት ዉል መቀላቀሉ ተረጋግጧል።
- ማሰታውቂያ -
በአራተኛ እና አምስተኛ ፈራሚነት ክለቡን የተቀላቀሉት ደግሞ የአማካይ ስፍራ ተጫዋቹ በኃይሉ ግርማ እና የአጥቂ ስፍራ ተጫዋቾቹ ሳሙኤል ሳሊሶ ሲሆኑ የዉድድር አመቱን ከመከላከያ ጋር ያሳለፉት ሁለቱ ተጫዋቾች አሁን ደግሞ የቀጣዩን የዉድድር አመት በሰበታ ከተማ መለያ የምንመለከታቸው ይሆናል።


