ኢትዮጵያ መድን በአዳማ 1ለዐ በተሸነፈበት ጨዋታ አሰልጣኝ ገብረመድኅን ሐይሌ ከጨዋታው በኋላ ምን አሉ ?
የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ሁለተኛው ዙር ዛሬ በተደረጉ አራት ጨዋታዎች ውድድሩ መመለሱ ይታወሳል። ሀዋሳ ላይ ማምሻውን በተደረገ ጨዋታ አዳማ ከተማ ኢትዮጵያ መድንን በቢኒያም ዐይተን ብቸኛ ጎል ማሸነፍ ሲችል በሜዳ ላይ ከታየው የዳኝነት ክፍተት ባሻገር ጨዋታው ከተጠናቀቀ በኋላ አሰልጣኝ ገብረመድኅን ሐይሌ በዕለቱ ዋና ዳኛ አባይነህ ሙላት እና ረዳቶቹ ላይ ከፍ ያለ ተቃውሞን ሲያሰሙ ተስተውሏል። አሰልጣኙም ከጨዋታው መጠናቀቅ በኋላ ከኦቢኤን ጋር በነበራቸው ቆይታ በዳኛው መሰደባቸውን ጠቁመዋል።
“ዳኞቹ ስነ ምግባር ይጎላቸዋል አንዳንዶቹ ዲሲፕሊን ይፈልጋል ዝም ብሎ ለእያንዳንዱ ነገሮች እየመለሱ አፀያፊ የሆኑ ነገሮችን መመለስም ሆነ መሳደብም አይችሉም ፣ ሲፈልግ ቢጫ አለው ቀይ አለው ከዛ ውጪ ግን አላስፈላጊ ነገሮች አይሆኑም። ሰዎች ነን ክብር አለን ለራሳችን ስለዚህ ሊንቀን እና ሊያንጓጥጠን አይገባም እንደዚህ አይነት ዳኞች ናቸው እየተመደቡ ችግር የሚፈጥሩት አንዳንዶቹ ስለዚህ ስርዓት መከባበር ጥሩ ነው ሁሉም የየራሱ የሆነ ስራ አለው አስፈላጊ ከሆነ ቢጫም ቀይም መስጠት ይችላል ማስጠንቀቅም ይችላል ከዛ ውጪ ግን መስደብ አይችልም እኔን ምንም ማለት አይችልም። “


