በCOVID-19 ሳቢያ መካሄድ ከነበረበት ወቅት በአንድ አመት ተገፍቶ በጃፓን በሚከናወነዉ የቶኪዮ ኦሎምፒክ ላይ ሀገራችን ኢትዮጵያ ከምትሳተፍባቸዉ የተለያዩ የስፖርት አይነቶች በተጨማሪም በኢንተርናሽናል ዋና ዳኛ በአምላክ ተሰማ እንደምትወከል ይታወቃል።
በተለያዩ አለም አቀፍ መድረኮች ሳይቀር በተሳተፈባቸው ዉድድሮች በሙሉ በጥሩ ብቃት ጨዋታዎችን በመምራት እና የሀገሩን ስም በበጎ መልኩ በማስጠራት አስደናቂ ስራን እየሰራ የሚገኘዉ በአምላክ አሁን ደግሞ የቢሊዮኖች አይን በሚመለከተወዉ እና በጉጉት በሚጠበቀዉ የቶኪዮ ኦሎምፒክ ላይ ጨዋታዎችን ለመምራት እና ብሎም ሀገራችንን ኢትዮጵያ ከአትሌቲክሱ በዘለለ በዳኝነቱ ለመወከል በነገዉ ጨዋታ ስራውን አንድ ብሎ የሚጀምር ይሆናል።
በኦሎምፒኩ ላይ ከሚከወኑ የስፖርት አይነቶች ዋነኛ የሆነዉ የወንዶች የእግርኳስ ጨዋታ ጅማሮዉን በነገዉ ዕለት የሚያደርግ ሲሆን በGroup A የተደለደሉትን እና በጉጉት የሚጠበቀዉን የፈረንሳይ እና ሜክሲኮ ጨዋታ ኢትዮጵያዊው ኢንተርናሽናል ዋና ዳኛ በአምላክ ተሰማ በአራተኛ ዳኝነት እንደሚመራ ሀትሪክ ስፖት ያገኘችው መረጃ ያመላክታል።
በሀገራችን ብሎም በአፍሪካ ደረጃ ቁጥር አንድ ከሚባሉ ኢንተርናሽናል ዳኞች መካከል ዋነኛዉ የሆነዉ እና የተለያዩ ጨዋታዎችን በአስደናቂ ብቃት በመምራት የሚታወቀው በአምላክ ተሰማ በተለያዩ አለም አቀፍ ዉድድሮች ላይ በመገኘት ታሪክ መስራቱ ይታወሳል ለአብነትም በ2018 የሩሲያ የአለም ዋንጫ ላይ መሳተፋ ይታወሳል። አሁን ደግሞ በተጠባቂዉ የቶኪዮ ኦሎምፒክ ላይ የምንመለከተው ይሆናል። ይሄም ሀገራችን ኢትዮጵያ በማትሳተፍባቸዉ የስፖርት ዉድድሮች ሁሉ በመገኘት በምርጥ ብቃት ጨዋታዎችን በማጫወት የሀገሩን ስም በየዉድድር መድረኩ ማስጠራት ችሏል።