በቅርቡ ከቅዱስ ጊዮርጊስ ጋር ተለያይቶ ወደ ወልዋሎ አዲግራት ያመራው ናትናኤል ዘለቀ ለቀድሞ ክለቡ የሰንብት እና የክለቡን ወቅታዊ ሁኔታዎች በተመለከተ በግል የፌስቡክ ገፁ ላይ መልዕክት አስተላልፏል።
በቅዱስ ጊዮርጊስ ቤት ከታዳጊ ቡድን ጀምሮ የተጫወተው እና በአመቱ መጀመሪያ ላይም የክለቡ ዋና አምበል ሆኖ ተሹሞ የነበረው ናትናኤል ከፈረሰኞቹ ጋር መለያየቱ ያልተጠበቀ ዜና እንደነበረም ይታወቃል።
መልዕክቱን በይቅርታ የጀመረው ናትናኤል “በመጀመሪያ ከክለባችን ጋር በዚህ ወቅት ልለያይ በመወሰኔ ትልቅ ይቅርታ እጠይቃለሁ” ብሏል።
ቅዱስ ጊዮርጊስ ከእናቴ ቤት ቀጥሎ ሁለተኛ ቤቴ ነው ያለው ናትናኤል እርሱን ከክለቡ ጋር ለመለያየት ገንዘብ በቂ ምክንያት ሊሆን አይችልም ሲል ተናግሯል።
- ማሰታውቂያ -
እስከ አሁን ድረስ ውሉን በሚያድስበት ወቅትም የክለቡ ልጅ ነው በሚል ያነሰ ገንዘብ እንደሚከፈለው ተናግሯል። “እስከዚች ቀን ድረስ ክለቤ ጋር ዉሌን ባደስኩ ጊዜ ሁሉ የቤት ልጅ ነዉ በሚል ሀሳብ ሁሉም ተጫዋቾች ከሚከፈላቸዉ ያነሰ ገንዘብ ነበር የሚከፈለኝ ፤ ይሄም ሀሳብ የቤቱን ልጆች በጣም ይጎዳል።”
ናትናኤል አክሎም ከውል ውጩ የሚገቡልኝ ቃሎች አሉ እነሱም እስከዛሬ ተደርገውልኝ አያውቁም ሲል ተናግሯል።
እንደ አንድ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤት እንዳደገ ተጫዋች የክለቡ ወቅታዊ ሁኔታ እንደሚያሳስበው እና ከዕለት ወደ ዕለት ቡድኑ ውስጥ የሚያየው ነገር አዕምሮውን እንደሚረበሽው ገልጿል።
ይህ ቦታ ለቅዱስ ጊዮርጊስ አይገባውም ያለው ናትናኤል ዘለቀ የክለቡን ወቅታዊ ሁኔታ ለማስተካከል የሚደረገው ጥረት አናሳ ሆኖ ስላገኘው ለመለያየት ከውሳኔ ስለመድረሱ ተናግሯል።
ናትናኤል አክሎም ለክለቡ ደጋፊዎች የአንድነት መልዕክት እንዲህ ብሎ አስተላልፏል። “በዚህ ሁሉ ዉስጥ ግን ምንም አይነት ሁኔታ የማይቀይራችሁ በከፍታም በዝቅታም ከቡድኑ ጋር ያልተለያችሁ ደጋፊዎች ለናንተ ትልቅ ክብር አለኝ። ግን በሀሳብም በድርጊትም የተለያያችሁ እዉነተኛ ደጋፊዎች እባካችሁ ቡድኔ ወደ በፊቱ አስፈሪነቱ ይመለስ ዘንድ የእናንተን አንድ መሆን ትልቁን ድርሻ ስለሚይዝ ቡድናችንን እሰከወዲያኛዉ ወደሚያሳድግ ሀሳብ አንድ ሁኑና ድረሱ።”
“ማንም ላይ ጥገኛ ያልሆነ ትልቁን ጊዮርጊስን ሰርታችሁ እንደምታሳዩኝ አልጠራጠርም። እኔ አንድ ቅዱስ ጊዮርጊስ ታሪኩን ያሳመረለት ተጫዋች ነኝ ቡድናችን ግን የሀገራችን እግር ኳስ ታሪክ ነዉ ስለዚህ ትኩረታችሁ ሁሉ ቡድናችን ላይ ይሁን።”
በመጨረሻም ስሙን ያልጠቀሰውን አንድ የክለቡን አመራር በተቸበት የመጨረሻ መልዕክቱ አብሮ የተጫወታቸውን ተጫዋቾች ፣ አሰልጣኞች ፣ የቢሮ ሰራተኞች ፣ አመራሮች እና ደጋፊዎች ምስጋናውን በማቅረብ ለክለቡ መልካም የውድድር ዘመን ተመኝቷል።


