የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በመጪው ቅዳሜ በአሜሪካ ከዲሲ ዩናይትድ ክለብ ጋር የወዳጅነት ጨዋታን ያደርጋል።
በአሰልጣኝ መሳይ ተፈሪ እየተመራ ለጨዋታው ዝግጅት በማድረግ ላይ የሚገኘው ብሔራዊ ቡድኑ በነገው ዕለትም 31 የልዑካን አባላትን በመያዝ ወደ አሜሪካ ያቀናል።
የብሔራዊ ቡድኑን ዝግጅት እና ከጉዞው ጋር የተያያዙ ጉዳዮችን በተመለከተ አሰልጣኝ መሳይ ተፈሪ እና የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ባህሩ ጥላሁን ማብራሪያ ሰጥተዋል።
ዋና ስራ አስፈፃሚው አቶ ባህሩ ጥላሁን በዋነኝነት ከቪዛ ጉዳይ ጋር በተያያዘ ሰፋ ያለ ገለፃ የሰጡ ሲሆን የተለያዩ ጥረቶችን በማድረግ ለሚጓዙት የልዑክ ቡድን አባላት ቪዛ ማግኘት ተችሏል ብለዋል።
- ማሰታውቂያ -

በአሰልጣኝ መሳይ ጥሪ ከተደረገላቸው 23 ተጫዋቾች መካከል 15 የሚሆኑድ አዲስ ቪዛ የጠየቁ ነበሩ ያሉት አቶ ባህሩ ከነዛም መካከል ሰባቱ አግኝተው ስምንቱ ግን ሊያገኙ አለመቻላቸውን ተናግረዋል።
ከአራት የአሰልጣኝ ቡድን አባላት ሁለቱ ፤ ከስድስት የስራ አስፈፃሚ አባላት ሶስቱ ቪዛ ያገኙ ሲሆን ሶስት(የቡድኑ ዶክተር ፣ የቡድኑ የስነ ምግብ ባለሙያ እንዲሁም የሚዲያ ኦፊሰር) ሌሎች አባላትም ቪዛ ማሳደሳቸውን ገልፀዋል።
35 የልዑካን ቡድን አባላትን ይዘን ለመሄድ ነበር ስምምነታችን ያሉት አቶ ባህሩ 31 የልዑካን ቡድን አባላት ወደ አሜሪካ ይጓዛሉ ብለዋል።
ምንም እንኳን ዋና ስራ አስፈፃሚው 31 አባላት ይጓዛሉ ቢሉም በሰጡት መረጃ 28 ግለሰቦች ሲሆኑ ቀሪ ሶስቱ እነማን እንደሆኑ አልገለፁም።
ይሄ ጨዋታ አንድ የወዳጅነት ጨዋታ ብቻ ተደርጎ መቆጠር የለበትም ያሉት አቶ ባህሩ ጥላሁን ለሶስት ዓመታት ያህል የተደረገ የቢዝነስ ስምምነት ሲሉ አፅንኦት በመስጠት ተናግረዋል።
በዚህም ጨዋታውን ስለሚያደርግ ብቻ 25 ሺህ ዶላር ጨዋታውን ካሸነፈ ደግሞ 50 ሺህ ዶላር በድምሩ ያለምንም ወጪ እስከ 75 ሺህ ዶላር ገቢን ያገኛል ብለዋል።
በጉዞው ከተካተቱት መካከል በተለይም የስራ አስፈፃሚ አባላቱን አስመልክቶ አቶ ባህሩ ጥላሁን ተከታዩን ብለዋል።
“የስራ አስፈፃሚ አባላት ይሄዳሉ ? አዎ ይሄዳሉ። የሚሄዱት ግን ምን አይነት ፋይዳን ሊያመጡ ነው የሚለው ወሳኝ ጥያቄ ነው። እሱን ለመመለስ የማርኬቲንግ ስራዎችንም ይሰራሉ። ከዲሲ ዩናይትድ የተለያዩ አመራሮች ጋርም በቀጣይ በሀገር ውስጥ አካዳሚዎችን ከመክፈት ጋር ሀሳብ አላቸው። የራሳቸውን ቡድን ከመመስረት አኳያ ብዙ ሀሳብ አላቸው። የራሳቸውን የምልመላ ቡድን ከማቋቋም ጋር ብዙ ሀሳብ አላቸው። ስለዚህ የሚሄደው አካል ጨዋታ አድርጎ የሚመለስ የቡድን አባላትን ብቻ ሳይሆን እንደዚህ አይነት ስትራቴጂክ በሆኑ ጉዳዮች ላይ ሊሰሩ የሚችሉ አመራሮች ወደ ስፍራው ይሄዳሉ።”
የሚሄዱት ትክክለኛ ቦታ ላይ ነው ሲሉ ያከሉት አቶ ባህሩ ጥላሁን የተጓዦች ስም ዝርዝር ይፋ መሆኑን የሀገር ሚስጥር የወጣ ነው ሲሉ ተናግረዋል።
“እውነት ለመናገር ፣ ግልፅ ለመሆን እንጥራለን። ግልፀኛ ለመሆን እየጣርን እንደሆነ ነው የሚሰማኝ ለምሳሌ ሰሞኑን ይፋ የሆነው ደግሞ የሀገር ሚስጥር የወጣ ነው የሚመስለው ፤ የትኬት ቡኪንግ ዝርዝር። ማን ምን እነደሆነ ማስረዳት እችላለሁ።”
አቶ ባህሩ ጥላሁን አክለውም በወጣው ዝርዝር ላይ የማይመለከተው ሰው ካለ ለመቀጣት ዝግጁ ነኝ ሲሉ ተናግረዋል።
የስራ አስፈፃሚው ኮሚቴ ተርሙን ለመጨረስ አንድ አመት ከአንድ ወር ያህል ይቀረዋል ፤ በቀጣይም አመትም ይህ ስራ አስፈፃሚ ቡድኑን ይዞ የሚጓዝ ይሆናል ብለዋል።
ፋይዳው በሚገባ ከግምት መግባት አለበት ሲሉም በማከል ለቀጣዩ አዲስ የስራ አስፈፃሚ እዳ አይደለም እየሰጠን ያለነው ሲሉ ተናግረዋል።
“አቶ ኢሳያስ ጅራ ወደ ለመጀመሪያ ጊዜ ሲመጡ 16 ሚልዮን ብር ዕዳ ነው የተቀበሉት ፤ የዛኛው የስራ አስፈፃሚ ነው ዕዳው ስለዚል እነሱጋር ይቅር አይደለም የተባለው። ተቋም ሁሌም ይኖራል ፤ ውስጡ ያሉ ሰዎች ግን ይቀያየራሉ።”
“እያወረስን ያለነው ዕዳ አይደለም የተሻለ ነገር ነው። ይሄ ወደ አሜሪካ የሚደረገው ጉዞ ትክክል አይደለም እንቀይረዋለን ማለት ይችላል የሚመለከተው አካል ማስቀጠልም ይችላል። እኛ ካደረግነው በላይም የተሻለ ስምምነት ማምጣት ይችላል። ለሀገር የሚጠቅም ለተጫዋቾች የሚጠቅም ነገር መስራት ይችላል።”
ከሲዳማ ቡና እና ያሬድ ባየል ጃር በተያያዘ አቶ ባህሩ ጥላሁን ይህንን ብለዋል።
“የሲዳማ ቡና እና የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ጉዳይ አላለቀም ፤ ካስ ሄዷል። ካስም ጉዳዩን እያየ እየመረመረ እኛም ምላሽ እየሰጠን ነው። በዚህ ሂደት ውስጥ አይመለከተውም ልንል የምንችልበት ምክንያት የለም። ሁለተኛ የብሔራዊ ቡድን ግዴት እና የክለብ ግዴታ ይለያያል። እኛ የጠራነው ለብሔራዊ ቡድን ግዴታ ነው።”
በሊግ ካምፓኒው በኩል የፋይናንስ ደንብ ጥሰት ፈፅመዋል በተባሉ ተጫዋቾች እና ክለቦች ላይ የተጣለውን ቅጣት አስመልክቶ በነበረው መግለጫ ላይ የተቀጡት ተጫዋቾች ለብሔራዊ ቡድንም አይጫወቱም ተብሎ ስለመነሳተለ ለቀረበላቸው ጥያቄም እኛ(የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን) አላልንም ሲሉ ገልፀዋል።
አቶ ባህሩ አክለውም ፌዴሬሽኑ በቅርቡ በአንድ የራዲዮ ጣቢያ ላይ የራሱን ፕሮግራም ሊጀምር ስለመሆኑ ገልፀዋል።


