የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በ2026 የዓለም ዋንጫ ማጣሪያ የምድብ አምስተኛ እና ስድስተኛ ጨዋታዎቹን በመጪው አርብ እና ሰኞ ከግብፅ እና ጅቡቲ ብሔራዊ ቡድኖች ጋር ያደርጋል። ብሔራዊ ቡድኑ ጨዋታዉን ወደሚያደርግበት ሀገር ሞሮኮ ዛሬ ለሊት ከመጓዙ በፊት በአሰልጣኙ ፣ በአምበሉ እና የፌዴሬሽኑ ዋና ስራ አስፈፃሚ መግለጫ ተሰጥቷል። የቡድኑ አምበል አስቻለው ታመነ በመግለጫው እንዳለው የብሔራዊ ቡድኑ ስብስብ ጥሩ ዝግጅት በማድረግ ላይ ይገኛል።በጥሩ ስሜት ነው ጨዋታዎቹንን የምናደርገውም ሲል ተናግሯል። የቡድኑ መንፈስን በተመለከተ እንደተናገረውም ከዚህ ቀደም ግብፅን ያሸነፍንበትን ጨዋታ ደግመን ተመልክተናል ያ ጨዋታም መነሳሻ የሚሆነን ነው ሲል ተናግሯል። በቀጣይም የተጋጣሚ ቡድን የተጋነነ ግምት ሰጥቶ ከማየት ጋር በተያያዘ ለቀረበለት ጥያቄ ተከታዩን ምላሽ ሰጥቷል።
“ቡድን አጋነን የምናይበት ነገር የለም አሁን ላይ ፤ አይታችሁ እንደሆነ ከቅርብ ጊዜያት በኋላ እንደከዚህ በፊቱ ጎል ስንት ይገባባችኋል ተብሎ የሚሄድ ብሔራዊ ቡድን የለንም።”
“በተሸነፍንባቸውም ባሸነፍንባቸውም ጨዋታዎች ፤ ግብፅም ከዚህ በፊት ሜዳው ላይ 1 ለ 0 ሲያሸንፈን ላይ ተቸግሮ ነው። ከዛ በፊት 2 ለ 0 አሸንፈን ስንመጣም እንዴት በልጠነው እንደነበር እናውቀዋለን።”
“የተለየ ግምት ሰጥተን ሞ ሳላህ ስላለ ምናምን ፣ የምንለው ነገር የለም። እግር ኳስ የሚፈቅደውን ነገር ነው የምናደርገው። የተጋነነ ግምት ሰጥተን የምንሄድበት አይደለም። በተሸነፍንባቸውም ጨዋታዎች ተቸግረው ነው።ግብፅ ከዚህ በፊት እናውቀዋለን በታሪክ ከኛ ጋር ያለውን ነገር ፤ ሜዳው ላይ ባሸነፈን ጨዋታም ሰዓት እስከመግደል የደረሱበት ሁኔታ አለ።”
- ማሰታውቂያ -
አክሎም ድሮ በነበረው ነገር ስለማይሆን ሜዳ ላይ እግርኳስ የሚፈቅደውን ነገር ለማድረግ ነው የምንሄደው የተለየ ግምት ሰጥተን አንሄድም ብሏል። አስቻለው ታመነ በተጨማሪም ከማህበራዊ ሚዲያ አጠቃቀም ጋር በተያያዘ በተጫዋቾች ላይ ተፅዕኖ መኖሩን ተናግሯል። ለዚህም ከጨዋታ በፊት ከተጫዋቾች ስልክ የመውሰድ ነገር ሊኖር እንደሚችል ገልጿል።
“እንደ እኛ ሀገር ተፅዕኖ እየፈጠረብን ያለው ማህበራዊ ሚዲያ ነው። የታወቀ ነው። ከአሰልጣኙ የሚሰጠን ነገር ይኖራል ፤ ከጨዋታ አንድ ቀን በፊት የቡድኑ የኑትሪሽን ባለሙያም የአሰልጣኞች ስታፍም ሆነው ስልክ የመውሰድ ልምድ ሊኖር ይችላል የሚል ዕምነት አለኝ ከጨዋታ በፊት ትኩረት እንዳናጣ ፤ ጨዋታው ላይ ትኩረት ማድረግ ስላለብን ፤ ይሄ እዛ ከሄድን በኋላ የሚሆን ነገር ነው። የአሰልጣኞች ስታፉ በሚሰጠን አቅጣጫ መሰረት እናደርጋለን የሚል ዕምነት አለኝ። እኔም እንደ አምበልነቴ ያን ነገር የምደግፈው አይደለም። ምክንያቱም በጣም ተፅዕኖ ከሚፈጥሩብን መካከል ማህበራዊ ሚዲያ ላይ የሚፃፉ ነገሮች እንደሆኑ እኔ በግሌ አምናለሁ።በጣም ተፅዕኖ ይፈጥራሉ።”
አሰልጣኝ መሳይ ተፈሪ እና አቶ ባህሩ ጥላሁን በመግለጫው ያነሷቸውን ነጥቦች ከደቂቃዎች በኋላ ወደ እናንተ እናደርሳለን።


