የ2017 ዓመተ ምህረት የኢትዮጵያ ዋንጫ የፍፃሜ ጨዋታ በነገው ዕለት በአዲስ አበባ ስታድየም ሲደረግ ሲዳማ ቡናን ከወላይታ ድቻ ያገናኛል።
ሲዳማ ቡና በታሪኩ ለመጀመሪያ ጊዜ በውድድሩ ፍፃሜ ተገኝቷል።
በሲዳማ ቡና የውድድሩ የዋንጫ ጉዞ ላይ ትልቅ ሚናን ከተወጡት ተጫዋቾች መካከል አንዱ መስፍን ታፈሰ ነው።
መስፍን ታፈሰ ስለ ሲዳማ ቡና የውድድር ዓመቱ የሊጉ እና የኢትዮጵያ ዋንጫ ጉዞ እንዲሁም የነገውን ተጠባቂ የፍፃሜ ጨዋታ በተመለከተ ከሀትሪክ ስፖርት ድህረገጽ ጋር ቆይታ አድርጓል።
- ማሰታውቂያ -
በፕሪሚየር ሊጉ የመጀመሪያ ዙር ጥሩ አልነበርንም የሚለው መስፍን በተለይም ከአሰልጣኝ ለውጡ በኋላ በቡድኑ ላይ በሜዳ ላይ የሚታይ ግልፅ ለውጥ አሳይቷል ብሏል።
ሲዳማ ቡና በኢትዮጵያ ዋንጫ ጉዞው ሶሎዳ አድዋ ፣ ስሁል ሽረ ፣ ሀድያ ሆሳዕና እንዲሁም መቻልን በመርታት ለፍፃሜው ደርሷል።
በዚህ ጉዞ ላይ ከባዱ ጨዋታ ሶሎዳ አድዋን የገጠመንበት ነው የሚለው መስፍን ያ ጨዋታ ጭንቀት ነበረው በቀጣይም ጠንካራ ተጋጣሚዎችን ድል አድርገን ነው ለዚህ የደረስነው ይላል።
“በኢትዮጵያ ዋንጫ አሪፍ ጉዞ ነው ያደረግነው ፤ የከፍተኛ ሊግ(ሶሎዳ አድዋ) ቡድኖችም አግኝተን ነበረ። በደንብ ፈትነውናል ብዬ ነው የማስበው ፣ እነሱ በጣም ነው የፈተኑን። በነሱ ፈተና ነው ለሁሉም እጅ ያልሰጠነው እና ለፍፃሜው ጠንክረን የደረስነው።”
ሲዳማ ቡና በሁለተኛው ዙር ሶሎዳ አድዋን መግጠሙ የሚታወስ ሲሆን በጨዋታው 2 ለ 0 ሲመራ ቆይቶ በመጨረሻ 15 ደቂቃዎች ሁለት ግቦችን በማስተናገድ በመለያ ምት 5 ለ 3 አሸንፎ ወደ ቀጣይ ዙር አልፏል።
ቡድኑ ከሶሎዳ አድዋው ጨዋታ ውጪ ያሉ ሶስቱን ጨዋታዎች ሀዋሳ ላይ ነበር ያደረገው ፤ ይህም በበርካታ ደጋፊዎች ፊት በመጫወታችን ተጠቃሚ አድርጎናል ብሏል መስፍን ታፈሰ።
“በደጋፊ ፊት ስትጫወት ምን ማድረግ እንዳለብህ ታውቃለህ። ደጋፊም ደግሞ ምን ጊዜም ያግዝሀል ይደግፍሀል። እና የነሱ መኖር ለኛ ጠቅሞናል ብዬ ነው የማስበው።”
አሊቶዎቹ ተከታታይ ስምንት የሊግ ጨዋታዎች ላይ ያለ ሽንፈት ከተጓዙ በኋላ ባለፉት ሁለት ተከታታይ ጨዋታዎች በመቀሌ 70 እንደርታ እና ኢትዮጵያ መድን ተሸንፈዋል።
ቡድኑ ከፍፃሜው ጨዋታ በፊት ተከታታይ ሽንፈቶች ማስተናገዱ ተፅዕኖ ያሳድርበት ይሆን ብለን ላቀረብንለት ጥያቄ መስፍን ተከታዩን መልስ ሰጥቷል።
“ከሽንፈት ስትመጣና አሸንፈህ ስትመጣ አንድ አይደለም። በእርግጥ ግን እኛ አዕምሮአችን ላይ ትኩረት ያደረግነው በኢትዮጵያ ዋንጫ ላይ ነው። በሁለቱም ላይ ትኩረት እናደርጋለን ግን በይበልጥ ደግሞ በአቋራጭ ዋንጫ ልናነሳ የምንችለው በኢትዮጵያ ዋንጫ ስለሆነ ከመጀመሪያውም ትኩረት ያደረግነው እሱን ነው።”
ከፕሪሚየር ሊጉ በላይ ለኢትዮጵያ ዋንጫው ነበር በአመቱ መጀመሪያ ላይ ትኩረት ያደረጋቹት የሚለው ቀጣዩ ጥያቄያችን ነበር።
“መጀመሪያ የሊጉን ዋንጫ ማሳካት ነው። ግን ነገሮች አልፈቀዱልንም። እና በጎን ደግሞ የኢትዮጵያን ዋንጫ አቅደን ነው የመጣነው ይሄ(ፕሪሚየር ሊግ) ከሆነ ሆነ ካልሆነ የኢትዮጵያ ዋንጫ ብለን ነው የተነሳነው።”
መስፍን ታፈሰ ሲዳማ ቡናን ከመቀላቀሉ በፊት በኢትዮጵያ ቡና በነበረው ቆይታ በአምናው የፍፃሜ ጨዋታ ቡናማውን ማልያ ለብሶ ዋንጫውን አሸንፏል።
በቅፅል ስሙ ጩንኬ የሚል መጠሪያ ያለው መስፍን በአምናው የፍፃሜ ጨዋታ የገጠመውን ወላይታ ድቻን ከ336 ቀናት በኋላ በተመሳሳይ መድረክ ይገጥማል።
“የዋንጫ ጨዋታ ስጫወት ለሶስተኛ ጊዜ ነው። ሀዋሳም እያለሁ ከፋሲል ጋር ተጫውቻለሁ። አምናም በኢትዮጵያ ቡና እያለሁም ከወላይታ ድቻ ጋር ተጫውቼ ዋንጫ በልቻለሁ። አሁንም ከባድ ጨዋታ ነው። እኛም ደግሞ በዛ ልክ እየተዘጋጀን ነው ብዬ አስባለሁ።”
ሌሎችም ዋንጫ የማሸነፍ ታሪክ ያላቸው ተጫዋቾች በቡድኑ አሉ የሚለው መስፍን ልምዳቸውን ለሌሎች ተጫዋቾች እያካፈሉ ያላቸውን ጠንካራ እና ደካማ ጎን እየተነጋገሩ በመዘጋጀት ላይ መሆናቸውን ጠቁሟል።
በዘንድሮው የውድድር ዘመን በርከት ያሉ በሊጉ ልምድ ያላቸውን ተጫዋቾች አስፈርሞ ዓመቱን የጀመረው ሲዳማ ቡና በኢትዮጵያ ዋንጫ ውድድር ላይ ለፍፃሜ ሲደርስ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው።
በክለቡ ዙሪያ ይህንን ዋንጫ ለማሳካት ከፍተኛ ተነሳሽነት እና ጉጉት አለ ሲልም መስፍን ተናግሯል።
“ራሳችንም ትልቅ ታሪክ ሰርተን ማለፍ እንፈልጋለን። ለደጋፊዎችም ደግሞ ይህ ትልቅ ነገር ነው። ለኛም ታሪክ ነው ለነሱም ደግሞ እንደ ታሪክ የሚወራ ነገር ስለሆነ ከዚህ አኳያ በደንብ እየደገፉን ነው። እግዚአብሔር ብሎ ደግሞ ዋንጫውን ብናነሳ በጣም ደስተኛ ነኝ።”
ሁለቱ የፍፃሜ ተፋላሚዎች በዘንድሮው የውድድር ዘመን በሊጉ ባደረጓቸው ሁለት ጨዋታዎች በአንዱ ሲዳማ ቡና ሲያሸንፍ በአንዱ ነጥብ ተጋርተዋል።
ሲዳማ ቡና ወላይታ ድቻን ለማሸነፍ በምን ደረጃ እየተዘጋጀ ነው ለሚለው ጥያቄ የተለየ ዝግጅት አናደርግም የመስፍን መልስ ነው።
“እኛ እንደ ሌሎች ጨዋታዎች ነው የምንዘጋጀው ፤ የዋንጫ ጨዋታ ስለሆነ እዚህ ጋር አቻ መውጣት የለም። ማሸነፍ እና ማሸነፍ ነው። ያን ነገር ስለምናውቅ ትኩረታችን ሁሉ ዋንጫው ላይ ነው። በአጠቃላይ ለማሸነፍ በጥሩ እየተዘጋጀን ነው።”
በሁለቱ ክለቦች ያለፉት ዘጠኝ የሊጉ የእርስ በርስ ግንኙነትች ሲዳማ ቡና በወላይታ ድቻ አልተሸነፈም። ይህ ተከታታይ ውጤት ለሲዳማ ቡና ተጫዋቾች ተጨማሪ መነቃቃትን ፈጥሮ ይሆን ? መስፍን ተከታዩን ብሏል።
“ይሄ ጥሎ ማለፍ ነው። እንደዚል የሚባል ነገር የለውም። ነገሮችን ተመልሰን ማየት የለብንም። በጨዋታው ላይ ስራችንን ሰርተን ያን ነገር ማስቀጠል ነው ያለብን።”
የውድድር ዓመቱ እምብዛም በግሌ ጥሩ አልነበረም ያለው መስፍን ታፈሰ ነገሮች እንዳሰብኩት አይደለም ፤ የተወሰነ ጫናም ነበር ሲል ገልጿል።
መስፍን አክሎም እግዚአብሔር ብሎ ዋንጫውን ብናነሳ በህይወቴ በጣም ደስተኛ የምሆንበት ቀን ነው ሲል ተናግሯል።
ጨዋታውን ለመመልከት እና ቡድናቸውን ለማበረታት በርካታ ቁጥር ያላቸው ደጋፊዎች የሲዳማ ቡና ደጋፊዎች በነገው ዕለት በአዲስ አበባ ስታድየም ይገኛሉ ተብሎ ይጠበቃል።
መስፍን ታፈሰም ተከታዩን መልዕክት ለደጋፊዎች አስተላልፏል።
“ከኛ ጎን ይሁኑ ፣ እኛም አናሳፍራቸውም። በነርሱ ነው እዚህ የደረስነው። እነሱ አቅም ነው የሚሆኑን እና ተጨማሪ አቅምም ነው የሚጨምሩልን ደስተኛ ነኝ እነርሱ በመምጣታቸው እና በነርሱ ፊት በመጫወታችን።”
የውጤት ግምት መግለፁ ይቅርብኝ ያለው መስፍን በእርግጠኝነት እናሸንፋለን በሚል ደምድሟል።
በመጨረሻም መስፍን ታፈሰ ጨዋታው በሰላም ተጀምሮ እንዲጠናቀቅ ለሁለቱም ክለብ ደጋፊዎች እና በጨዋታው ተሳታፊ ለሆኑት መልዕክቱን አስተላልፏል።
“እግር ኳስ በርግጥ የፍቅር ነው። እየተዝናናህ የምታየው ነው። እንደዚህ አይነት ነገሮች ደስ አይሉም። እኛ ጋር ያለውንም ነገር እናስተካክላለን። ነገሮች ከኛም ከዳኛም ስለሚሄዱ መጠንቀቅ አለብን። ስፖርት ውስጥ ስሜታዊ ትሆናለህ። በእርግጥ ምንም ሊፈጠር ይችላል ግን መለስ ብለህ ስታይ ነው ሁሉም ነገር ታሪክ ሆኖ የሚያልፈው ከዚህ አኳያ በኛም በነሱም በኩል ሜዳ ላይ ጥሩ ነገር እናሳያለን ብዬ አስባለሁ።”


