እግር ኳስን ከትውልድ አካባቢው መቱ ከጀመረ በኋላ በከፍተኛ ሊጉ ወሎ ኮምቦልቻ ያሳየው ብቃት ግን ወደ ፕሪምየር ሊጉ እንዲመጣ አድርጎታል።
በጅማ አባጅፋር የጀመረው የሀገሪቱ ትልቁ የሊግ ዕርከን ተሳትፎው በመቀጠልም ሰበታ ከተማ ፣ ባህርዳር ከተማ እያለ አሁን ዘለግ ያለ ቆይታ እያደረገ ለሚገኝበት ኢትዮጵያ መድን አድርሶታል።
ራሱን ከጊዜ ወደ ጊዜ እያበቃ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ቋሚ የግብ ዘብ ለመሆን የበቃው የአንድ ሜትር ከዘጠና ሁለት ሴንቲ ሜትር ባለቤቱ አቡበከር ኑራ በተጠናቀቀው የ2017 የውድድር ዘመን ክለቡ መድን የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ዋንጫን በታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ሲያነሳ ለክለቡ የስኬት ቁልፎች መሐል አንዱ መሆን ከመቻል አልፎ የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ የውድድር ዘመኑ ምርጡ ግብ ጠባቂ ተብሎ የዋንጫ እና ዳጎስ ያለ የገንዘብ ሽልማትንም ተጎናፅፏል።
ዋልያዎቹ ግብፅን በገጠሙበት ጨዋታ ባሳየው አስደናቂ ብቃት በርካቶች ልብ ውስጥ የቀረው አቡበከር ኢትዮጵያ መድን ሀገራችንን ወክሎ በተሳተፈበት የካፍ ቻምፒየንስ ሊግ ጨዋታ ላይ በደርሶ መልስ በድምር ውጤት የዛንዚባሩን ምላንዴግን 4ለ3 በማሸነፍ ወደ ቀጣዩ ዙር ቡድኑ ማለፉን መስከረም 17/2018 በሁለተኛው ማጣሪያው ሲያረጋግጥ ከሜዳው ውጪ በነበረው ጨዋታ ላይ ሜዳ ውስጥ ግጭት አስተናግዶ በግራ እግሩ ላይ የመሰንጠቅ ጉዳት ገጥሞት የነበረው ቁመታሙ ግብ ጠባቂ ከተደረለት ህክምና በኋላ እግሩ ላይ ጄሶ የገባለት ሲሆን እስኪጠነክርም ከሦስት ወራት በላይ በጉዳት ከሜዳ ርቆ ቆይቶ አሁን ላይ ከጉዳቱ አገግሞ ልምምድ ስለ መጀመሩ ተጫዋቹ አረጋግጦልኛል።
“የገጠመኝ የአጥንት መሰንጠቅ ነበር በግራ እግሬ ላይ ሦስት ወራትን ርቄያለሁ አሁን ሙሉ ለሙሉ ወደ ልምምድ ተመልሻለሁ ያው ትንሽ ፍርሀት ነው እንጂ ሰሞኑን እመለሳለሁ።” ሲል ገልፆልኛል።


