በቀጣይ አመት የትግራይ ክልል ከለቦች የማይሳተፋ ከሆነ በሊጉ የሚሳተፈዉ አንዱ ክለብ አዳማ ከተማ መሆኑ ታዉቋል።
መሪዉን አዳማ ከተማ ከ ሀምበሪቾ ያገናኘዉ የእለቱ ሁለተኛ ጨዋታ በተያዘለት መርሀግብር መሰረት ከቀኑ 7:00 ሲል ተጀምሯል።
ለሁለቱም ቡድኖች ወሳኝ በነበረዉ ጨዋታ ከጨዋታው ጅማሮ አንስቶ ማራኪ ጨዋታን ከተደጋጋሚ የግብ ሙከራዎች ጋር ሲያሳዩን የነበሩት አዳማ ከተማዎች ገና በጨዋታው ጅማሮ 11ኛዉ ደቂቃ ላይ የተገኘውን ቅጣት ምት ኤሊያስ ማሞ ወደ ግብነት ቀይሮ አዳማ ከተማን መሪ ማድረግ ችሏል።

ከግቧ መቆጠር በኋላ በይበልጥ ተጠናክረዉ የቀጠሉት አዳማዎች በ25ኛዉ ደቂቃ ላይም ግብ ማስቆጠር የሚችሉበትን እድል ቢያገኙም አብዲሳ ጀማል ሳይጠቀምበት ቀርቷል።
በጨዋታውም አማካይ ክፍል ላይ ጥሩ ሲንቀሳቀስ የነበረዉ በቃሉ ገነነ በራሱ ጥረት ተጫዋቾችን አታሎ በማለፍ ከርቀት ግሩም ግብ በማስቆጠር ክለቡ መሪነቱን ወደ 2ለ0 ከፍ እንዲያደርግ አስችሏል።
በሀምበሪቾ በኩል መሀል ላይ ኳስ መስርተዉ በአንድ ሁለት ቅብብል ወደ ተቃራኒ ቡድን የግብ ክልል ለመድረስ ያደርጉት የነበረዉ ጥረት እምብዛም ዉጤታማ ሁኖ አልተመለከትንም። የጨዋታዉ ሂደት በዚሁ ቀጥሎ በአዳማ ከተማ መሪነት ወደ እረፍት አምርተዋል።

ከዕረፍት መልስ ተሻሽለው የቀረቡት ሀምበሪቾዎች በ77ኛዉ ደቂቃ ላይ በአላዛር ኦቴ አማካኝነት ግብ ማስቆጠር ችለዉ ነበር። ከግቧ መቆጠር በኋላ በተደጋጋሚ ወደ አዳማ ከተማ የግብ ክልል መድረስ ቢችሉም ሁለተኛ ግብ ማስቆጠር ሳይችሉ ቀርተዋል። በአንፃሩ አዳማ ከተማ ግቧ ከተቆጠረችባቸዉ በኋላ ወደ ኋላ በማፈግፈግ ዉጤቱን አስጠብቀው ለመዉጣት ሲሞክሩ ተስተዉሏል።

የጨዋታው ሂደትም በዚህ ቀጥሎ አዳማ ከተማ ሀምበሪቾ ዱራሜን 2ለ1 በማሸነፍ አንድ ጨዋታ እየቀረዉ በቀጣይ አመት የትግራይ ክልል ክለቦች በሊጉ የማይሳተፉ ከሆነ እነርሱን በመተካት በሊጉ ተሳታፊ የሚሆን ክለብ ይሆናል ።
አስተያየት ይስጡ