በዕለቱ ሁለተኛ ጨዋታ የተገናኙት ኢትዮጵያ ቡና እና ወልቂጤ ከተማ ጠንካራ የሜዳ ላይ ፉክክር አድርገው ቡናማዎቹ በዊልያም ሰለሞን ብቸኛ ግብ አሸንፈው ወጥተዋል ።
ወልቂጤ ከተማ አዲስ አበባ ከተማን ባሸነፉበት ጨዋታ ከተጠቀሙት ቋሚ አስራአንድ አንድ ቅያሪ ብቻ በማድረግ ውሀብ አዳምስን ያሰለፉ ሲሆን በኢትዮጵያ ቡና በኩል ግን ድሬደዋ ከተማን ባሸነፉበት ጨዋታ የነበረውን ቋሚ አሰላለፍ ምንም ሳይቀይሩ ወደ ሜዳ ገብተዋል ።
በሳቢ የሜዳ ላይ እንቅስቃሴ የተጀመረው ጨዋታ በሁለቱም በኩል ወደፊት በሚሄዱ ኳሶች ታጅቦ ነበር የተጀመረው ። በተለይም ቡናማዎቹ በመስመር የሚያደርጓቸው ቅብብሎችን ወደ ሳጥን በመውሰድ የግብ ዕድሎችን ለመፍጠርም የቻሉበት ነበር ። በአራተኛው ደቂቃ ላይ አቡበከር ናስር ከአስራት ቱንጆ የደረሰውን ኳስ ለማስቆጠር ያደረገው ጥረት በተከላካዮች ተመልሶበታል ።
- ማሰታውቂያ -
የወልቂጤ ከተማ የፊት መስመር ተጫዋቾች የኢትዮጵያ ቡና ኳስ መስርቶ ለመውጣት የሚያደርጉትን ጥረት በመግታት የግብ ዕድሎችን ለመፍጠር የጣሩ ሲሆን 12ኛ ደቂቃ ላይ ያሬድ ታደሰ ያደረገው ሙከራ ለዚህ ተጠቃሽ ነበር ።
22ኛ ደቂቃ ላይ ዊልያም ሰለሞን ከቀኝ መስመር የደረሰውን ኳስ በሳጥን ውስጥ አግኝቶ ለማስቆጠር ያደረገው ሙከራ በተስፋዬ ነጋሽ ከሽፎበታል ። ወዲያው የተጀመረው ኳስ ጌታነህ ከበደ አግኝቶ ወደ ግብ ያደረገው ሙከራ በግቡ አግዳሚ ተመልሶበታል ። በቀጣዮቹ የመጀመሪያው አጋማሽ ደቂቃዎች ላይ ተመጣጣኝ የማጥቃት እንቅስቃሴ በሁለቱም ቡድኖች በኩል ያስመለከትን ቢሆንም ያለምንም ግብ ሊጠናቀቅ ችሏል ።
የሁለተኛው አጋማሽ ግብ ለማስተናገድ አምስት ያህል ደቂቃዎች ብቻ ነበር የፈጁበት ። ዊልያም ሰለሞን ከአቡበከር ናርር የደረሰውን ኳስ 50ኛ ደቂቂላይ በማስቆጠር ቡናማዎቹን መሪ ማድረግ ቻለ ።
68ኛ ደቂቃ ላይ አቡበከር ናስር ያደረገበትን ሙከራ ያመከነው የወልቂጤ ከተማው ግብ ጠባቂ ሲልቭያን ግቦሆ ከዕለቱ የመሀል ዳኛ ጋር በፈጠረው አለመግባባት በሁለቴ የቢጫ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል ።
የቁጥር የበላይነትን ያገኙት ቡናማዎቹ በቀጣዮቹ ደቂቃዎች ብልጫ ወስደው መጫጫየቻሉ ሲሆን በተለይም ለአቡበከር በሚደርሱ እና በዊልያም ሰለሞን የግል ጥረቶች ተደጋጋሚ የግብ ሙከራዎችን ቢያደርጉም ኳስን ከመረብ ማገናኘት ሳይችሉ ቀርተዋል ። በወልቂጤ ከተማ በኩል በጥቂት አጋጣሚዎች በተለይም በመልሶ ማጥቃት በሚሄዱ ፈጣን ኳሶች ግቦችን ለማግኘት ቢሞክሩም ግብ ማግኘት ሳይችሉ ጨዋታው በኢትዮጵያ ቡና 1 ለ 0 አሸናፊነት ተጠናቋል ።
ውጤቱን ተከትሎም ኢትዮጵያ ቡና ነጥቡን 14 በማድረስ በግብ ክፍያ ተበልጦ በደረጃ ሰንጠረዡ 4ኛ ላይ ሲቀመጥ ወልቂጤ ከተማ በበኩሉ በ12 ነጥብ ወደ 6ኛ ተንሸራቶል ።