በስምንተኛው ሳምንት የሶስተኛ ቀን ውሎ ቀዳሚ ጨዋታ በወላይታ ድቻ እና በቅዱስ ጊዮርጊስ መካከል ተደርጎ ሄኖክ አዱኛ ከርቀት መቶ ባስቆጠረው ብቸኛ ግብ ፈርሰኞቹ ሙሉ ሶስት ነጥቦ ይዘው ወጥተዋል ።
ወላይታ ድቻዎች በሰባተኛው ሳምንት በባህርዳር ከተማ በተሸነፉበት ጨዋታ ከተጠቀሙት ቋሚ አስራ አንድ የሶስት ተጫዋቾች ቅያሪ በማድረግ ወንድወሰን አሸናፊ ፤ አንተነህ ጉግሳ ፤ ደጉ ደበበ እና እድሪስ ሰዒድን ቀይረው ሲያስገቡ በቅዱስ ጊዮርጊስ በኩል ከአዳማ ከተማ ጋር አቻ ከተለያየው ቡድን ከነአን ማርክነህን ብቻ በመቀየር ጨዋታውን ጀምረዋል ።

በጨዋታው ቅዱስ ጊዮርጊሶች በኳስ ቁጥጥሩ የተሻለ በመሆን ጨዋታውን የጀመሩ ሲሆን በሙከራ ደረጃም የተሻለ እንቅስቃሴን ማድረግ ችለው ነበር ።
12ኛው ደቂቃ ላይ አማኑኤል ገብረሚካኤል ከአቤል ያለው በሳጥን ውስጥ ሆኖ የደረሰውን ኳስ አረጋግቶ ወደ ግብ ቢሞክረውም በግብ ጠባቂው ተመልሶበታል ። ከአራት ደቂቃዎች በኋላ አቤል ያለው ከከንአን ማርክነህ የተቀበለውን ኳስ ይዞ በሳጥን ውስጥ በመግባት ያደረገው ሙከራ በግብ ጠባቂው በድጋሚ ተመልሶበታል ።

ጫና በማሳደር የቀጠሉት ፈረሰኞቹ በሀያ ሶስተኛ ደቂቃ ላይ ከነአን ማርክነህ ያገኘውን ጥሩ አጋጣሚ ወደ ግብ ሳይቀይረው መቅረቱ ለቅዱስ ጊዮርጊስ የሚያስቆጭ አጋጣሚ ነበር ። በቀጣዮቹ ደቂቃዎች ላይ ቅዱስ ጊዮርጊስ በወላይታ ድቻ ሜዳ ላይ አብዛኛው ጊዜ በማሳለፍ ግብ ለማኘት ያደረጉት ጥረት ውጤታማ ሳይሆን ቀርቷል ። የኳስ ቁጥጥር ብልጫ የተወሰደባቸው የጦና ንቦቹ በተወሰኑ አጋጣሚዎች በመልሶ ማጥቃት የግብ ዕድሎችን ለመፍጠር ጥረቶችን ቢያደርጉም የመጀመሪያው አጋማሽ በሁለቱም በኩል ግብ ሳይቆጠርበት ተጠናቋል ።

በሁለተኛው አጋማሽ በአብዛኛው በመጀመሪያው አጋማሽ የታየው የሜዳ ላይ እንቅስቃሴ የታየበት ሲሆን ወላይታ ድቻዎች አጥቂያቸውነሰ ስንታየሁ መንግስቱን ማጣታቸው በብዙ መልኩ ክፍተት እንደፈጠረባቸው በግልፅ ታይቷል ። ፈረሰኞቹ በአጋማሹ ያደረጉት የግብ ሙከራ 48ኛው ደቂቃ ላይ በእስማኤል ኦጎሮ አማካኝነት ሲሆን ከያብስራ የተሻገረለትን ኳስ ተቆጣጥሮ ወደ ግብ ቢሞክረውም በወላይታ ድቻ ተከላካይ ተመልሶ የማዕዘን ምት ሆኗል ።

በመልሶ ማጥቃት ዕድሎችን ለመፍጠር እየተንቀሳቀሱ የነበሩት የጦና ንቦቹ 56ኛ ደቂቃ ላይ በእድሪስ ሰይድ እና በምንይሉ ወንድሙ ጥሩ ቅብብል ወደ ግብ ያደረጉት ሙከራ ለጥቂት ከግቡ አናት በላይ ወቷል ። ግብ ለማግኘት የወላይታ ድቻን የተከላካይ መስመር በተደጋጋሚ ሲያንኳኩ የነበሩት ፈረሰኞቹ 65ኛ ደቂቃ ላይ በሄኖክ አዱኛ ግሩም ግብ መሪ መሆን ቻሉ ። በአቤል ያለው ከማዕዘን የተሻገረለው ኳስ በወላይታ ድቻ ተከላካይ ሲመለስ ያገኘው የመስመር ተከላካዩ ሄኖክ አዱኛ አክርሮ በመምታት አስቆጠረ ።

በቀጣዮቹ ደቂቃዎች ፈረሰኞቹ ያስቆጠሩትን ግብ አስጠብቀው ለመውጣት የተጫወቱበት ነበር ። የጦና ንቦቹ የአቻነቷን ግብ ለማግኘት ያደረጉት ጥረት በአጥቂ መስመራቸው ክፍተት ምክንያት ሳይሳካላቸው ቀርቷል ። በስተመጨረሻም ጨዋታው በቅዱስ ጊዮርጊስ 1 ለ 0 አሸናፊነት ተጠናቀቀ ።

ውጤቱን ተከትሎም ቅዱስ ጊዮርጊስ ነጥቡን 14 በማድረስ ብዙ ግብ ባስቆጠረ በሚለው 3ኛ ደረጃ ላይ ሲቀመጥ ወላይታ ድቻ በበከሉ በ13 ነጥብ 5ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል ።
አስተያየት ይስጡ