በስድስተኛው ሳምንት ሶስተኛ ቀን የመጀመሪያ ጨዋታ ፈረሰኞቹ ሀዋሳ ከተማን ሁለት ለአንድ በማሸነፍ ደረጃቸውን አሻሽለዋል።
በአምስተኛ ሳምንት ፈረሰኞቹ ከሲዳማ ቡና ጋር በነበራቸው ጨዋታ ከተጠቀሟቸዉ የመጀመሪያ አስራ አንድ ተጫዋቾች መካከል የአራት ተጫዋቾችን ለዉጥ አድርገው ወደ ሜዳ ሲገቡ በአንፃሩ በሀይቆቹ ሀዋሳ ከተማዎች በኩል ደግሞ ከሀድያ ሆሳዕና ጋር በነበራቸው ጨዋታ ከተጠቀሟቸዉ ቋሚ አስራ አንድ ተሰላፊዎች መካከል የሶስት ተጫዋቾችን ለዉጥ በማድረግ ወደ ሜዳ ገብተዋል።
ከጨዋታው ጅማሮ አንስቶ ጥሩ የሚባል እንቅስቃሴን ማድረግ የቻሉት ፈረሰኞቹ የመጀመርያ ግባየውን በ15ኛው ደቂቃ ላይ ማስቆጠር ችለዋል። ከግራ መስመር በኩል የተሻገረውን ኳስ የመስመር አጥቂው አቤል ያለው ለፊት አጥቂው እስማኤል ኡሮ አጎሮ አቀብሎት በጥሩ አቋቋም ላይ ይገኝ የነበረው አጥቂው ኳሷን ወደ ግብ በመላክ ፈረሰኞቹን መሪ ያደረገች ግብ ማስቆጠር ቻለ።
- ማሰታውቂያ -
ከግቧ መቆጠር በኋላ በተሻለ መነሳሳት ጨዋታውን መቆጣጠር የቻሉት ቅዱስ ጊዮርጊሶች ሁለተኛ ግባቸዉን ለማስቆጠር በተደጋጋሚ የሀይቆዩቹን የግብ ክልል ሲጎበኙ ተስተዉሏል። በተለይ ደግሞ በ32ኛዉ ደቂቃ ላይ አጥቂዉ ኢስማኤል ከአማኑኤል ገ/ሚካኤል የተቀበለውን ኳስ በድጋሚ ወደ ግብ አክርሮ በመላክ ሁለተኛ ግብ ለማስቆጠር ቢሞክርም ግብ ጠባቂዉ መሀመድ ሙንታሪ በድንቅ ብቃት ተቆጣጥሯታል።
በሀዋሳ ከተማዎች በኩል የመጀመሪያውን አጋማሽ በተቀዛቀዘ የጨዋታ መንገድን ሲያሳልፉ የተመለከትን ሲሆን ፤ በጨዋታው መሀልም አማካዩ ፀጋአብ ዩሀንስ በጉዳት ምክንያት በሄኖክ ድልቢ ተቀይሮ ለመዉጣት ተገዷል። በዚህ ሂደት የቀጠለው የሁለቱ ክለቦች ጨዋታም የመጀመሪያው አጋማሽ ሊጠናቀቅ ጥቂት ደቂቃዎች በቀሩት ሰዓትም ሁለተኛ ግብ ተስተናግዶበታል። በዕለቱ ጥሩ ሲንቀሳቀስ የነበረዉ አቤል ያለዉ በድጋሚ ለኢስማኤል ኳሷን አቀብሎት አጥቂው እንደምንም አስቆጥሯታል። በዚህም መሰረትም የመጀመሪያው አጋማሽ በፈረሰኞቹ የሁለት ለዜሮ መሪነት ተጠናቋል።
በሁለተኛው አጋማሽ በተሻለ የጨዋታ መንገድ የተመለሱት ሀዋሳ ከተማዎች በ50ኛዉ ደቂቃ ላይ የመጀመሪያ ግባቸዉን ማስቆጠር ችለዋል። ሱለይማን ሀሚድ ኤፍሬም አሻሞ ላይ የሰራዉን ጥፋት ተከትሎ የተገኘውን ፍፁም ቅጣት ምት አዲስ አለም ተስፋየ አስቆጥሮ ክለቡን ወደ ጨዋታው ለመመለስ ጥረት አድርጓል።
ከዚች ግብ መቆጠር በኋላ በድጋሚ የግብ እድልን አግኝተዉ የነበሩት ሐይቆቹ በኤፍሬም አሻሞ አማካኝነት ሁለተኛ ግብ ማስቆጠር የሚችሉበትን ዕድል ቢያገኙም ሳይጠቀሙበት ቀርተዋል። የጨዋታዉ ሰዓት እየገፋ በሔደ ቁጥር የማጥቃት ሀይላቸዉን እያጠናከሩ የሄዱት ፈረሰኞቹ በተደጋጋሚ በፊት አጥቂዉ ኢስማኤል አማካኝነት ተደጋጋሚ የግብ ዕድሎች ማግኘት ችለዉም ነበር።
በሀይቆቹ በኩል በተለይ በተደጋጋሚ ረዥዥም ኳሶችን ወደ ፈረሰኞቹ የግብ ክልል በመላክ የአቻነት ግብ ለማስቆጥር ቢጥሩም ዉጥናቸዉ ሰምሮ ተጨመሪ ግብ ማግኘት ሳይችሉ ቀርተው ጨዋታው በፈረሰኞቹ የሁለት ለአንድ አሸናፊነት ተጠናቋል።