የቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ የአምስተኛ ሳምንት ጨዋታዎች ዛሬ ሲጀመሩ በመጀመሪያው ጨዋታ የተገናኙት በዘርዓይ ሙሉ የሚመራው ሀዋሳ ከተማ በሙሉጌታ ምህረት የሚመራው ሀድያ ሆሳዕና ጨዋታቸውን ያለምንም ግብ አጠናቀዋል ።

ሁለቱ ተጋጣሚዎች በአራተኛው ሳምንት ከተጠቀሙት ቋሚ አሰላለፍ ሶስት ሶስት ቅያሪዎችን ያደረጉ ሲሆን ሀዋሳ ከተማ በቃሉ ገነነ ፤ መድኃኔ ብርሃኔ እና ዳዊት ታደሰ እንዲሁም ሀድያ ሆሳዕና ፍቅረየሱስ ተ/ብርሀን ፤ ፀጋዬ ብርሃኔ እና ደስታ ዋሚሾን ወደ ቋሚ 11 አስገብተው ጨዋታቸውን ጀምረዋል ።
በጨዋታው የመጀመሪያ አጋማሽ በሀድያ ሆሳዕና በኩል ኳስ ተቆጣጥረው በመጫወት ወደ ፊት ለመሄድ ጥረቶችን ያደረጉ ሲሆን በሀዋሳ ከተማ በኩል ደግሞ በፈጣን መልሶ ማጥቃት የሀድያ ሆሳዕናን የተከላካይ መስመር ለማስጨነቅ ሞክረው ነበር ነገር ግን በሁለቱም በኩል ይህ ነው ሊባል የሚችል የግብ ሙከራ ለረጅም ደቂቃዎች አልተመለከትንም ነበር ።

36ኛው ደቂቃ ላይ ሀዋሳ ከተማዎች ለግብ የቀረበ ሙከራ ማድረግ ችለው ነበር ። መስፍን ታፈሰ በሳጥን ውስጥ ከኤፍሬም አሻሞ መሬት ለመሬት የደረሰውን ኳስ አግኝቶ ቢሞክረውም ኳሱወደ ውጪ ወቶበታል ። ከሰባት ደቂቃዎች በኋላም በድጋሚ መስፍን ታፈሰ የሻገረለትን ኳስ አስቆጠረው ተብሎ ሲጠበቅ ግብ ጠባቂው ሶሆሆ ሜንሱህ በፍጥነት ወጥቶ ሊመልስበት ችሏል ።
የሁለተኛው አጋማሽ ከተጀመረ ገና ሁለት ደቂቃ እንደሆነው የሀዋሳ ከተማው ፀጋሰው ድማሙ በፀጋዬ ብርሀኑ ላይ በሰራው ጥፋት በቀጥታ የቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናበተ ። ይህም ሀዋሳ ከተማዎች ቀሪዎቹን ደቂቃዎች በ10 ተጫዋቾች ለማካሄድ ተገደዋል ።

በአጋማሹ ሀድያ ሆሳዕናዎች በሙከራ ረገድ የሻለ እንቅስቃሴ ማድረግ ችለውም ነበር ። በተለይም 4 ቁጥሩ ፀጋዬ ብርሀኑ 57ኛ ደቂቃ ላይ በሳጥኑ ውስጥ ያገኘውን ኳስ በግራ እግሩ ወደ ግብ ሲሞክረው በሙንታሪ ተመልሶ የማዕዘን ምት ሆኗል ። ይኸው ተጫዋች 64ኛ ደቂቃ ላይም ከሳጥን ውጪ አክርሮ ወደ ግብ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም በድጋሚ በግብ ጠባቂው ተመልሶበታል ።

ጨዋታው ሊጠናቀቅ አራት ደቂቃዎች አካባቢ ሲቀሩት አበባየሁ ዮሀንስ ከረጅም ርቀት ወደ ግብ የመታው ከባድ ኳስ መሀመድ ሙንታሪ በድንቅ ብቃት ወደ ውጪ አውጥቶታል ።
ጨዋታውም 0 ለ 0 ሲጠናቀቅ ሀዋሳ ከተማ ነጥቡን ሰባት ሲያደርስ ሀድያ ሆሳዕና በበኩሉ ነጥቡን ወደ ሶስት አሳድጓል ።
አስተያየት ይስጡ