በኢትዮጵያ ዋንጫ የሩብ ፍፃሜ የሦስተኛ ቀን መርሀግብር ኢትዮጵያ መድን 2ለ0 በሆነ ውጤት ቤንች ማጂ ቡናን በመርታት ወደ ግማሽ ፍፃሜው አልፏል።

በአዲስ አበባ ስታዲየም በሦስተኛ ቀኑ በቀጠለው የኢትዮጵያ ዋንጫ ጨዋታ ኢትዮጵያ መድን የከፍተኛ ሊጉን ቤንች ማጂ ቡናን በመርታት ወደ ቀጣዩ ዙር ማለፍ ችሏል። አሰልጣኝ አብርሀም ሐይሌን ከቀጠረ በኋላ በከፍተኛ ሊጉ ምድብ ሀ ሁለተኛውን ዙር በጥሩ ብቃት የቋጨው ቤንች ማጂ ቡና ከዕረፍት በፊት በፕሪምየር ሊጉ ክለብ ያስተናገዳቸው ሁለት ጎሎች ከውድድሩ ውጪ እንዲሆኑ አድርጓቸዋል።

በሁለተኛው ዙር የመድን አዲስ ፈራሚ የሆኑ ተጫዋቾች ጎል ባስቆጠሩበት ጨዋታ 25ኛው ደቂቃ ላይ ረመዳን የሱፍ ከግራ የሜዳው ክፍል የሰጠውን ኳስ ሳሙኤል ሳሊሶ መረቡ ላይ ሲያሳርፋት 35ኛው ደቂቃ ላይ ደግሞ ከማዕዘን ምት ሳሙኤል ሳሊሶ አሻምቶ ጋናዊው ሁለገብ ተጫዋች ቤንጃሚን ኮቴ በግንባር ገጭቶ ሌላኛዋን ጎል በማከል ጨዋታው 2ለ0 በአሰልጣኝ ገብረመድኅን ሐይሌው መድን አሸናፊነት ተቋጭቷል።

ዛሬ አሸናፊ መሆን የቻለው በቀጣይ በግማሽ ፍፃሜውን መቐለ 70 እንደርታን የሚያስተናግድ ሲሆን የግማሽ ፍፃሜ ቀሪ ጨዋታ ደግሞ ነገ በነገሌ አርሲ እና ሲዳማ ቡና መካከል ይደረጋል።
አስተያየት ይስጡ