የቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ አራተኛ ሳምንት ጨዋታዎች በዛሬው ዕለት ሲጀምሩ ሻምፕየኑ ቅዱስ ጊዮርጊስ ተከታታይ የአሸናፊነት ጉዞውን ያስቀጠለበትን ውጤት አዳማ ከተማን በመርታት አስመዝግቧል ።
በአዳማ ከተማ በኩል በሶስተኛው ሳምንት ሀዋሳ ከተማን ባሸነፉበት ጨዋታ ላይ የነበረው የመጀመሪያ አሰላለፍ ሙሉ ለሙሉ ሲጠቀሙ በቅዱስ ጊዮርጊስ በኩል በሳምንቱ ሲዳማ ቡናን በሰፊ ውጤት ባሸነፉበት ጨዋታ ላይ ከነበረው ምርጥ 11 አማኑኤል ገብረሚካኤልን በዳዊት ተፈራ ምትክ ተክተው ጨዋታውን ጀምረዋል ።
የጨዋታው የመጀመሪያ አጋማሽ በሁለቱም በኩል በፈጣን እንቅስቃሴ ተጀምሮ ነገር ግን በተጀመረበት ሂደት መቀጠል ያልቻለ ነበር ።
- ማሰታውቂያ -
በአዳማ ከተማ በኩል በኳስ ቁጥጥሩ በአንፃራዊነት የተሻለ በመሆን ወደ ፊት ለመድረስ ጥረቶችን ያደረጉበት ሲሆን በቅዱስ ጊዮርጊስ በኩል ኳሶችን በፈጣን ወደ ተጋጣሚ የግብ ክልል በመላክ ዕድሎችን ለመፍጠር ሞክረዋል ።
በተለይም በመጀመሪያው አጋማሽ ከሜዳ ላይ እንቅስቃሴ ባለፈ በተጫዋቾች መካከል የነበሩ ሹክቻዎች በተደጋጋሚ ጨዋታው በዳኛው ፊሽካ እንዲቋረጡ አድርገዋል ። ከነዚህም መካከል ገና በ10ኛው ደቂቃ ላይ የአዳማ ከተማው ተከላካይ ሚሊዮን ሰለሞን ጉዳት አጋጥሞት በዳንኤል ደምሴ ተቀይሮ ለመውጣት ተገዷል ።
በ15ኛው ደቂቃ ላይ ቸርነት ጉግሳ በረጅም የደረሰውን ኳስ በቀኝ መስመር ይዞ ገብቶ ፈረሰኞቹን ቀዳሚ ለማድረግ ያደረገው ጥረት በግብ ጠባቂው ተመልሷል ።
በ27ኛው ደቂቃ ላይ ደግሞ አዳማ ከተማዎች በሳጥን ውስጥ ያገኙትን ኳስ በአግባቡ ሳይጠቀሙበት ቀርተዋል ። ብዙም ጠንካራ የግብ ሙከራዎች ያላስተናገደው የመጀመሪያ አጋማሽም ያለ ግብ ፍፃሜውን አግኝቷል ።
የሁለተኛው አጋማሽ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ከመጀመሪያው አጋማሽ የተሻለ የግብ ዕድሎች የታዩበት እና ሶስት ያህል ግቦች የተስተናገዱበት ነበር ።
ሻምፕየኖቹ በጨዋታው መሪ መሆን የቻሉትን ግብ በ51ኛው ደቂቃ ላይ ሲያስቆጥሩ ልማደኛው ግብ አነፍናፊ እሰማኤል ኦሮ ኦጎሮ የግቡ ባለቤት መሆን ችሏል ። ረመዳን የሱፍ በረጅም የላከውን ኳስ ቢንያም በላይ አግኝቶ ሳይጠቀምበት ቢቀርም ቶጎአዊው አጥቂ ኳሱን ከመረብ ጋር አዋህዷል ።
ግብ ያስተናገዱት አዳማ ከተማዎች በመሀል ክፍል ላይ ብልጫ በመውሰድ ወደ ፈረሰኞቹ የግብ ክልል ለመድረስ ጥረቶችን ቢያደርጉም የተጋጣሚያቸውን የኋላ መስመር አልፈው ቻርለስ ሉክዋጎን ለመፈተን ተቸግረው ቢቆዩም ከ15 ደቂቃዎች በኋላ ኳስ እና መረብን አገናኝተዋል ።
ከቀኝ መስመር የተነሳው ኳስ መሀል ሲሻገር ከአብዲሳ ጀማል የተቀበለው ዳዋ ሆቴሳ ከጨረቃዋ በቀጥታ ወደ ግብ በመምታት በቻርለስ ሉክዋጎ መረብ ላይ ማሳረፍ ችሏል።
አዳማ ከተማዎች ወድያው ሶስት የማጥቃት ባህሪ ያላቸውን ተጫዋቾችን በመቀየር ከጨዋታው ሶስት ነጥብ ይዘው ለመውጣት በቀጣዮቹ ደቂቃዎች ላይ ጥረቶችን አድርገዋል ።
በፈረሰኞቹ በኩል በተለይም በመስመሮች በኩል በሚደረጉ እንቅስቃሴዎች የማሸነፊያ ግብ ለማስቆጠር ያደረጉት ጥረት በመጨረሻም ፍሬ አፍርቶላቸዋል ። በውድድር አመቱ ለመጀመሪያ ጊዜ በቋሚ አሰላለፍ ተካቶ የተጫወተው አማኑኤል ገብረሚካኤል በሳጥን ውስጥ አዲስ ተስፋዬን ለማለፍ በሚጥርበት ወቅት በተሰራበት ጥፋት የፍፁም ቅጣት ምት አግኝተዋል ።
የፍፁም ቅጣት ምቱንም እስማኤል ኦሮ አጎሮ በማስቆጠር ክለቡን አሸናፊ ሲያደርግ በወድድር አመቱም በሊጉ ያስቆጠራቸውን የግብ ብዛቶች 8 ማድረስ ችሏል ።
ከተጨማሪ አራት ደቂቃዎች በኋላ ጨዋታው በቅዱስ ጊዮርጊስ የ2 ለ 1 አሸናፊነት ፍፃሜውን አግኝቷል ።
በአምስተኛ ሳምንት ጨዋታዎች በመጪው ጥቅምት 14(ሰኞ) አዳማ ከተማ ኢትዮ ኤሌክትሪክን 10:00 ጀምሮ ሲገጥም በተከታዩ ቀን በተመሳሳይ ሰዓት ቅዱስ ጊዮርጊስ ከፋሲል ከነማ ይጫወታል ።