በዕለቱ ቀዳሚ ጨዋታ ባሳለፍነዉ ሳምንት በሊጉ መቆየቱን ያረጋገጠዉ ወልቂጤ ከተማ አዳማ ከተማን 1ለ0 በሆነ ዉጤት ማሸነፍ ችሏል ።
በዋና ዳኛ ቢኒያም ወርቅአገኘሁ መሪነት ቀን ዘጠኝ ሰዓት በጀመረዉ ጨዋታ ገና በጊዜ ወጣቱ የፊት መስመር ተጫዋች ቢኒያም አይተን በአዳማ ከተማ በኩል ከቦና አሊ የተቀበለዉን ኳስ ወደ ግብ ሞክሮ የግቡ ቋሚ በመለሰበት ሙከራ የጨዋታ እንቅስቃሴያቸዉን የጀመሩ ሲሆን ፤ በዚህ ሂደትም በተደጋጋሚ ዘደ ወልቂጤ ከተማ የግብ ክልል በመድረስ እና የመስመር ተጫዋቾቻቸዉን በመጠቀም ዕድሎችን በመፍጠር ግቦችን ለማስቆጠር ሲጥሩ ፤ በተቃራኒው ሰራተኞቹ ደግሞ በእንቅስቃሴ ረገድ በሚቆራረጡ ኳሶች እና የመሐል ላይ ቅብብሎች ለመጫዋት ሲሞክሩ ተስተዉሏል።
በዚህ ሂደት በቀጠለዉ ጨዋታዉ በ21ኛዉ ደቂቃ ላይ ተከላካዩ መሳይ ጳውሎስ ቢኒያም አይተን ላይ ጥፋት መስራቱን ተከትሎ የተሰጠዉን ፍፁም ቅጣት ምት ቦና አሊ መትቶት የነበረ ቢሆንም ነገር ግን ግብ ጠባቂዉ ፋሪስ አለሙ ኳሷን አምክኗታል። ጫና ፈጥረዉ መጫወታቸዉን የቀጠሉት አዳማዎች በ31ኛዉ ደቂቃ ላይ ደግሞ በጀሚል ያቆብ አማካኝነት ግሩም ሙከራ አድርገዉ የነበረ ቢሆንም ነገር ግን የግቡ ቋሚ ኳሷን መልሷታል።
- ማሰታውቂያ -
ደካማ የነበሩት ክትፎዎቹ ከደቂቃዎች በኋላ ደግሞ የፍፁም ቅጣት ምት ማግኘት ችለዉ ጋዲሳ መብራቴም ፔናሊቲውን መምታት ችሎ የነበረ ቢሆንም ነገር ግን ኳሷ ወደ ዉጭ ወጥታለች። ከዕረፍት መልስ አዳማ ከተማዎች የማጥቃት ሀይላቸዉን አሻሽለዉ ወደ ሜዳ የገቡ ሲሆን ፤ በተቃራኒው ብልጫ የተወሰደባቸዉ ወልቂጤ ከተማዎች ደግሞ ያን ያህል ተጠቃሽ ሙከራዎችን ማድረግ ሳይችሉ ቀጥለዉ ይባስኑ በ61ኛዉ ደቂቃ ላይ አልሀሺምን በሁለተኛ ቢጫ በቀይ ካርድ አጥተዉታል።
በዚህ ሂደት በቀጠለዉ ጨዋታ በ10 ተጫዋቾች እየተጫወቱ የነበሩት ወልቂጤዎች በ72ተኛዉ ደቂቃ ላይ ከማዕዘን ተመስገን በጅሮንድ ያሻገረዉን ኳስ ተከላካዮች ሲመልሱት ያገኘዉ አዳነ በላይነህ ወደ ግብነት ቀይሮ ክለቡ ወልቂጤ ከተማ አመቱን በድል መደምደም የቻለበትን ዉጤት እንዲያስመዘግብ አድርጓል።
በዕለቱ ሁለተኛ ጨዋታ ሁለቱ መውረዳቸዉን ያረጋገጡት ሻሸመኔ እና ሀምበሪቾ ባደረጉት ጨዋታ ሻሸመኔ ከተማ 3ለ1 በሆነ ዉጤት ማሸነፍ ችሏል።
በተመጣጣኝ የሜዳ ላይ እንቅስቃሴ እና በሙከራ ረገድ ተቆጥቦ በጀመረዉ የሁለቱ ክለቦች የምሽቱ ጨዋታ ገና በጊዜ ተመስገን አሰፋ ከቅጣት ምት በሞከራት ኳስ ሀምበሪቾን ቀዳሚ ለማድረግ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም በሻሸመኔዉ ግብ ጠባቂ ኬኒ ሰይድ ድንቅ ብቃት ኳሷ መክናበታለች።
በዚህ ሂደት የጀመረዉ ጨዋታም ለ18 ያክል ደቂቃዎች ቀጥሎ ግብ ተቆጥሮበታል ፤ በዚህም ሳጥን ውስጥ የሻሸመኔዉ አጥቂ ስንታየሁ መንግስቱ ያቀበለዉን ኳስ ሱራፌል ሙሉዎርቅ ወደ ግብነት ቀይሮ ክለቡን ሻሸመኔ ከተማ መሪ ማድረግ ችሏል። ከግቧ መቆጠር በኋላ በተደጋጋሚ ጫና ፈጥረዉ መጫወት የቀጠሉት ሻሸመኔዎች ዳግም በ37ተኛዉ ደቂቃ ግብ አክለዋል። በዚህም አብዱልቃድር ናስር ከመሐል የተቀበለዉን ኳስ ለአጥቂዉ ስንታየሁ አቀብሎት አጥቂዉም ሁለተኛዋን ጎል በጎሩም ብቃት አስቆጥሯል።
ከሰባት ደቂቃዎች በኀላ ዳግም አጥቂዉ ስንታየሁ ተጫዋቾችን ጭምር በማለፍ ለራሱ ሁለተኛ ለክለቡ ደግሞ ሶስተኛ ግብ አስቆጥሮ አጋማሹ በሻሸመኔ ከተማ ሶስት ለዜሮ መሪነት ተገባዷል። ከዕረፍት መልስ ሁለቱም ክለቦች ተመጣጣኝ የመሐል ሜዳ እንቅስቃሴን እያስመለከቱን የቀጠሉ ቢሆንም ነገር ግን ዕድሎችን በመፍጠር እና ግብ በማስቆጠሩ ረገድ ውስንነቶች ተስተዉሎባቸዋል።
በዚህ ሂደት በቀጠለዉ ጨዋታም መደበኛዉ ዘጠና ደቂቃ ተጠናቆ በጭማሪዉ ደቂቃ 90+5 ላይ የሻሸመኔዉ ተከላካይ ኢብሳ ኳስ በዕጅ መንካቱን ተከትሎ የተሰጠዉን ፍፁም ቅጣት ምት ኤፍሬም አሻሞ አስቆጥሮ ጨዋታዉ በሻሸመኔ ከተማ 3ለ1 አሸናፊነት ተጠናቋል።