በበርካታ የደጋፊዎች ድባብ ታጅቦ ቀን 10:00 ሲል በጀመረዉ የዕለቱ ወሳኝ ጨዋታ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ተጋጣሚዉን ማሸነፍ የሚችል ከሆነ ዋንጫዉን በታሪኩ ለመጀመሪያ ጊዜ ማሸነፉን የሚያረጋግጥ መሆኑን ተከትሎ በተለየ የጨዋታ መንገድ እንቅስቃሴ ማድረጋቸዉን የጀመሩ ሲሆን ፤ በዚህም ገና በጊዜ ማለትም በ3ተኛዉ ደቂቃ ግብ ማስቆጠር ችለዋል። ከወደ ቀኝ መስመር በኩል ከቲካ ጀማ ለቀኝ ተመላላሹ ሱለይማን ሀሚድ የሰጠዉን ኳስ ተጫዋቹ ወደ ግብነት ቀይሮ ክለቡን ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ገና በመባቻዉ መሪ ማድረግ ችሏል።
ከግቧ መቆጠር በኋላ አሁንም ይበልጥኑ በተለየ ተነሳሽነት ጨዋታዉን መከወን የቀጠሉት ባንኮች ከግማሽ ሰዓት በኋላ ዳግም በአዲስ ግደይ አማካኝነት ከሳጥን ውጭ ግሩም ግብ አስቆጥረዉ ጨዋታዉን ገና በጊዜ ሁለት ለዜሮ መምራት ቀጥለዋል። በተቃራኒው ተቀዛቅዘዉ እና በተጋጣሚያቸው ብልጫ ተወስዶባቸዉ ጨዋታቸዉን የጀመሩት መድኖች መደበኛዉ አርባ አምስት ሊጠናቀቅ አምስት ደቂቃ ብቻ ሲቀረዉ በወገኔ ገዛኸኝ አማካኝነት ከሳጥን ውጭ ግሩም ሙከራ ቢያደርጉም የግብ ጠባቂዉ ፍሬዉ ጌታሁን ቅልጥፍና ግን ኳሷ ወደ ዉጭ እንድትወጣ አድርጓታል።
በሁለተኛዉ አጋማሽ ያን ያህል ሙከራ ባላስመለከተን የጨዋታዉ እንቅስቃሴ በ68ተኛዉ ደቂቃ ላይ ባሲሩ ዑመር ከአዲስ ግደይ በተቀበለዉ ኳስ ግሩም ሙከራ ማድረግ ችሎ የነበረ ቢሆንም ነገር ግን የግቡ ቋሚ ከልክሎበታል። በዚህ ሂደት እየወረደ የቀጠለዉ ጨዋታ ግብ ሳይቆጠርበት በአሰልጣኝ በፀሎት ልዑልሰገድ ቡድን ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሁለት ለዜሮ አሸናፊነት ተጠናቋል።
- ማሰታውቂያ -
ዉጤቱን ተከትሎ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በታሪኩ ለመጀመሪያ ጊዜ የሊጉን ዋንጫ ማሸነፍ ሲችል ፤ በተመሳሳይ ሰዓት በሀዋሳ ሰዉ ሰራሽ ሜዳ ድሬዳዋ ከተማን የገጠመዉ እና ለዋጫዉ ዕድል የነበረዉ የአሰልጣኝ ገ/ክርስቶስ ቢራራ ቡድን መቻል አንድ ለዜሮ በሆነ ዉጤት ጨዋታውን ማሸነፍ ቢችልም ነገር ግን የዋንጫዉ ባለድል መሆን ሳይችል ቀርቶ አመቱን በሁለተኝነት አጠናቋል።