የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 21ኛ ሳምንት ጨዋታዎች በዛሬው ዕለት በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታድየም መደረግ ጀምረዋል።
የዕለቱ ቀዳሚ መርሐግብር በኢትዮ ኤሌክትሪክ እና ኢትዮጵያ ቡና መካከል ተደርጎ በኢትዮጵያ ቡና አሸናፊነት ተጠናቋል።
የቡናማዎቹን ብቸኛ ግብ ጋናዊው ኮንኮኒ ሀፍዝ በ18ኛው ደቂቃ ላይ ከመረብ አሳርፏል። ኮንኮኒ ሀፍዝ ላስቆጠረው ግብ ኳሱን አመቻችቶ ያቀበለው አማካዩ ይታገሱ እንዳለ ነው።
የውድድር ዓመቱን አምስተኛ ግብ ያስቆጠረው ጋናዊው አጥቂ ባሳለለፍነው ሳምንትም ኢትዮጵያ ቡና ስሁል ሽረን ሲረታ ብቸኛውን ግብ ማስቆጠሩ ይታወሳል።
- ማሰታውቂያ -
ኢትዮጵያ ቡና በውድድር ዓመቱ ለ11ኛ ጨዋታ ግብ ሳያስተናግድ ያጠናቀቀበት ሲሆን ባለፉት አራት ተከታታይ ጨዋታዎችም የዳንላንድ ኢብራሂም መረብ አልተደፈረም።
የነፃነት ክብሬው ቡድን ነጥቡን 32 በማድረስም ከመሪው ኢትዮጵያ መድን ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ ሶስት ዝቅ አድርጓል።
ኢትዮ ኤሌክትሪክ በበኩሉ ከመጀመሪያው ዙር የመጨረሻ አራት ጨዋታዎች በሶስቱ አሸንፎ የነበረ ቢሆንም በሁለተኛው ዙር ግን ተከታታይ ሽንፈት አስተናግዷል።
በ22ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ኢትዮጵያ ቡና ከ ሀዋሳ ከተማ እንዲሁም ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከ ስሁል ሽረ በመጪው እሁድ የካቲት 30 ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
አመሻሽ 12:00 ጀምሮ በተደረገው ጨዋታ ደግሞ ሀድያ ሆሳዕና እና ሲዳማ ቡና ነጥብ ተጋርተዋል።
በጨዋታው መስፍን ታፈሰ አሊቶዎቹን ገና በሶስተኛው ደቂቃ ላይ መሪ ማድረግ ቢችልም ከሁለት ደቂቃዎች በኋላ እዮብ አለማየሁ ያስቆጠረው ግብ ከቤራዎቹን አቻ አድርጓል።
አስቀድሞ በመጀመሪያ አምስት ደቂቃዎች ውስጥ ሁለት ግቦችን ያስተናገደው ጨዋታው በቀሪ ደቂቃዎች ግብ ሳያስተናግድ ተጠናቋል።
ለሳምንታት በመሪዎቹ ተርታ የሚገኘው ሀድያ ሆሳዕና ካለፉት ስድስት ጨዋታዎች በአንዱ ብቻ ያሸነፈ ሲሆን ማግኘት ከሚችለው 18 ነጥቦች ማሳካት የቻለው 6 ብቻ ነው።
ሲዳማ ቡና በበኩሉ ተከታታይ ሶስተኛ የአቻ ውጤቱን ያስመዘገበ ሲሆን ሽረ እንደስላሴን ያሸነፈበት ጨዋታ ካለፉት ስምንት ጨዋታዎች ያስመዘገበው ብቸኛ ድሉ ነው።
ሀድያ ሆሳዕና ነጥቡን 32 ቢያደርስም ኢትዮ ኤሌክትሪክን በረታው ኢትዮጵያ ቡና በንፁህ ግቦች ተበልጦ 3ኛ ደረጃ ላይ ለመቀመጥ ሲገደድ ሲዳማ ቡና ምንም እንኳን በነበረበት 11ኛ ደረጃ ቢቀጥልን ነጥቡን 25 አድርሷል።
በቀጣይ ሳምንት ጨዋታዎች ሀድያ ሆሳዕና ከ ባህርዳር ከተማ እንዲሁም ሲዳማ ቡና ከ አዳማ ከተማ የፊታችን ሰኞ መጋቢት 1 ቀን ይጫወታሉ።


