በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 17ኛ ሳምንት የሶስተኛ ቀን ጨዋታዎች በዛሬው ዕለት ሲደረጉ ሀዋሳ ከተማ ከ103 ቀናት በኋላ ሶስት ነጥቦችን አሳክቷል።
አመሻሽ 12:00 ጀምሮ በተደረገው ጨዋታ የሊጉ የሁለት ጊዜ ሻምፒዮን ሀዋሳ ከተማ ከመሪዎቹ ተርታ የሚገኘው መቻልን 1 – 0 አሸንፏል።
በጨዋታው ኤርትራዊው ዓሊ ሱሌማን በ54ኛው ደቂቃ ላይ ያስቆጠረው ግብ ለሀይቆቹ አሸናፊነት በቂ ሆኗል።
ለበርካታ ቀናት እና ሳምንታት ከድል የራቀው ሀዋሳ ከተማ የመጨረሻ ድሉን ጥቅምት ዘጠኝ ቀን ሀድያ ሆሳዕናን 2 – 1 በረታበት ጨዋታ ላይ ማስመዝገቡ ይታወሳል።
- ማሰታውቂያ -
ውጤቱን ተከትሎ ሀዋሳ ከተማ ነጥቡን 15 በማድረስ ደረጃውን ወደ 16ኛ ከፍ ማድረግ ችሏል።
ድል አድርጎ የሊጉን መሪነት ዳግም መረከብ የሚችልበትን ዕድል ያመከነው መቻል በ27 ነጥብ 3ኛ ደረጃ ላይ ለመቆየት ተገዷል።
ቡድኑ የዛሬውን ጨምሮ ካለፉት ተከታታይ አራት ጨዋታዎች ማግኘት ከሚገባው 12 ነጥቦች ማግኘት የቻለው ሶስቱን ብቻ ነው።
በ18ኛ ሳምንት መርሐግብር ሀዋሳ ከተማ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሲጫወት መቻል በበኩሉ አራፊ ቡድን ነው።
በዕለቱ በቀዳሚነት ከቀን 9:00 ጀምሮ በተደረገው ጨዋታ ወልዋሎ አዲግራት ለተከታታይ ሶስተኛ ጨዋታ ከሽንፈት የራቀበትን ውጤት አስመዝግቧል።
ቡድኑ በ55ኛው ደቂቃ ላይ በዳዋ ሆጤሳ አማካይነት በፍፁም ቅጣት ምት በተቆጠረ ግብ ለ13 ያህል ደቂቃዎች መሪ መሆን ችሎ ነበር።
በ68ኛው ደቂቃ ላይ ግን ፍቃዱ አለሙ ኤልፓን አቻ ያደረገ ግብ ከመረብ አሳርፏል።
ዳዋ ሆጤሳ ከ259 ቀናት እንዲሁም ፍቃዱ አለሙ ከ225 ቀናት በኋላ በሊጉ ግብ ያስቆጠሩበት ጨዋታ ሆኗል።
ውጤቱን ተከትሎ ወልዋሎ አዲግራት ነጥቡን 6 ሲያደርስ ኢትዮ ኤሌክትሪክ በበኩሉ 19 አድርሷል።
በ18ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ወልዋሎ አዲግራት ከድሬዳዋ ከተማ እንዲሁም ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከአዳማ ከተማ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።


