የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 17ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን መርሐግብሮች በዛሬው ዕለት ሲደረጉ የአዲስ አበባዎቹ ክለቦች ቅዱስ ጊዮርጊስ እና ኢትዮጵያ ቡና ድል ቀንቷቸዋል።
ከ9:00 ጀምሮ በተደረገው ቀዳሚው ጨዋታ ፈረሰኞቹ የጦና ንቦቹን 2 – 0 አሸንፈዋል።
እስከ 76ኛው ደቂቃ ድረስ ያለ ግብ በተጓዘው ጨዋታ አብዱ ሳሚዮ ቻታኮራ ቅዱስ ጊዮርጊስን መሪ ያደረገ ግብ በ77ኛው ደቂቃ ላይ አስቆጥሯል።
ከስምንት ደቂቃዎች በኋላ ደግሞ አማኑኤል ኤርቦ ሁለተኛ ግብ አክሎ ጨዋታው በቅዱስ ጊዮርጊስ የ2 – 0 አሸናፊነት እንዲጠናቀቅ አድርጓል።
- ማሰታውቂያ -
አማኑኤል ኤርቦ በጨዋታው ያስቆጠረውን ግብ ተከትሎ በውድድር ዓመቱ ያስቆጠራቸውን የግብ ብዛቶችንም 6 ማደረስ ችሏል።
ፈረሰኞቹ በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርስቲ ስታድየም ያላቸውን መልካም ውጤት ያስቀጠሉበት ውጤት ሆኖ ተመዘግቧል።
ቡድኑ ነጥቡን 28 በማድረስም በመጪው አርብ ጨዋታውን ከሚያደርገው የሊጉ መሪ ኢትዮጵያ መድኅን ያለውን የነጥብ ልዩነት አንድ ብቻ አድርጓል።
በ18ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ቅዱስ ጊዮርጊስ ከኢትዮጵያ ቡና ሲጫወት ወላይታ ድቻ በበኩሉ ከመቀሌ 70 እንደርታ ይጫወታል።
በዕለቱ ሁለተኛ መርሐግብር ደግሞ ኢትዮጵያ ቡና ባህርዳር ከተማን ከስድስት ዓመታት በኋላ ያሸነፈበትን ድል አስመዝግቧል።
ቡናማዎቹ 3 – 1 ባሸነፉበት ጨዋታ ኮንኮኒ ሀፍዝ በ6ኛ እና 36ኛ ደቂቃዎች ላይ እንዲሁም አንተነህ ተፈራ በ89ኛው ደቂቃ ላይ ግቦቹን አስቆጥረዋል።
አንተነህ ተፈራ ከያሬድ ብርሀኑ እና አህመድ ሁሴን በመቀጠል በውድድር ዓመቱ 7ኛ የሊግ ግብ ያስቆጠረ ተጫዋች ሆኗል።
በጨዋታው ሙጂብ ቃሲም ባህርዳር ከተማን ከሽንፈት ያልታደገች ግብ በ15ኛው ደቂቃ ላይ ማስቆጠር ችሎ ነበር።
ኢትዮጵያ ቡና ድሉን ተከትሎ ነጥቡን 22 በማድረስ ወደ ሰባተኛ ደረጃ ከፍ ማለት ችሏል።
ባህርዳር ከተማ በበኩሉ ወደ ሊጉ መሪዎች ከፍ ማለት የሚችልበትን ዕድል ሳይጠቀም በመቅረቱ በ23 ነጥቦች 5ኛ ደረጃ ላይ ለመቆየት ተገዷል።
በቀጣይ ሳምንት ጨዋታዎች ኢትዮጵያ ቡና ከቅዱስ ጊዮርጊስ ሲጫወት ባህርዳር ከተማ አራፊ ቡድን ነው።


