የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 16ኛ ሳምንት የሶስተኛ ቀን ጨዋታዎች በዛሬው ዕለት ተደርገው ሁለቱም ጨዋታዎች በአቻ ውጤት ተጠናቀዋል።
በዕለቱ ቀዳሚ መርሐግብር ከቀን 9:00 ጀምሮ በተደረገው ጨዋታ በደረጃ ሰንጠረዡ 2ኛ እና 5ኛ ላይ የነበሩት መቻል እና ባህርዳር ከተማ ነጥብ ተጋርተዋል።
1 – 1 በተጠናቀቀው ጨዋታ አቤል ነጋሽ በ16ኛው ደቂቃ ላይ ከሳጥን ውጪ በግራ እግሩ አክሮ በመምታት ያስቆጠረው ድንቅ ግብ ጦሩን ለ23 ደቂቃዎች መሪ አድርጓል።
በ39ኛው ደቂቃ ላይ ግን ቸርነት ጉግሳ በግሩም ሁኔታ የመቻልን ተጫዋቾች ሸውዶ ከሳጥን ውጪ የመታው ኳስ ከመረቡ አርፎ የጣና ሞገዶቹን አቻ አድርጓል።
- ማሰታውቂያ -
በቀሪ የመጀመሪያ አጋማሽም ሆነ በሁለተኛው አጋማሽ ተጨማሪ ግብ ያላስተናገደው ጨዋታ ለሁለቱም አንድ አንድ ነጥብ አጋርቶ ተጠናቋል።
መቻል ከሊጉ መሪ ኢትዮጵያ መድኅን ጋር በነጥብ መስተካከል የሚችልበትን ዕድል ሳይጠቀምበት ቀርቷል። በተመሳሳይ ባህርዳር ከተማም በጨዋታው ድል ማድረግ ቢችል ከሊጉ መሪ ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ አራት ማጥበብ ይችል ነበር።
በቀጣይ ሳምንት መርሐግብር መቻል ከሀዋሳ ከተማ ባህርዳር ከተማ ደግሞ ከኢትዮጵያ ቡና ይጫወታሉ።
በዕለቱ ሁለተኛ መርሐግብር የተገናኙት ቅዱስ ጊዮርጊስ እና ሀዋሳ ከተማም በተመሳሳይ 1 – 1 ተለያይተዋል።
በጨዋታው 41ኛ ደቂቃ ላይ ፍፁም ጥላሁን ከበረከት ወልዴ የደረሰውን ኳስ ለቢንያም ፍቅሩ አቀብሎት ቢንያም ፍቅሩ ኳስና መረብን በማዋሀድ ቡድኑን መሪ አድርጓል።
የመጀመሪያው አጋማሽ መጠናቀቂያ በተቃረበበት ወቅት ግን አቤኔዘር ዮሐንስ ከርቀት አክርሮ የመታውን ኳስ በአስደናቂ ሁኔታ አስቆጥሮ ሐይቆቹን አቻ አድርጓል።
ውጤቱን ተከትሎ ቅዱስ ጊዮርጊስ ነጥቡን 25 ሲያደርስ ሀዋሳ ከተማ በበኩሉ 12 ነጥብ ላይ መድረሽ ችሏል።
በ17ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ቅዱስ ጊዮርጊስ ከወላይታ ድቻ እንዲሁም ሀዋሳ ከተማ ከመቻል ይጫወታሉ።


