የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 16ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ዛሬም በሁለተኛ ቀን መርሐግብር ቀጥለው ሁለት ጨዋታዎች በአ.ሳ.ቴ.ዩ. ስታድየም ተደርገዋል።
አመሻሽ 12:00 ጀምሮ የተደረገው እና በብዙ የተጠበቀው የኢትዮጵያ መድኅን እና የኢትዮጵያ ቡና ጨዋታ በኢትዮጵያ መድኅን የ1 – 0 አሸናፊነት ተጠናቋል።
መደበኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ሊጠናቀቅ ስድስት ያህል ደቂቃዎች ሲቀሩት የቀድሞው የቅዱስ ጊዮርጊስ እና ወልቂጤ ከተማ ተጫዋች አቡበከር ሳኒ መድኅንን አሸናፊ ያደረገች ግብ አስቆጥሯል።
የገብረመድህን ኃይሌው ቡድን ተከታታይ 5ኛ ድሉን በማስመዝገብ መሪነቱን ሲያጠናክር በውድድር ዘመኑ አስረኛ ግብ ያላስተናገደበት ጨዋታ ሆኗል።
- ማሰታውቂያ -
ኢትዮጵያ መድኅን ዘንድሮ በአንድ ጨዋታ ብቻ ሽንፈት ያስተናገደ ብቸኛው ቡድን ሲሆን የሊጉን መሪነት ተከታዮቹ እስኪጫወቱ በሶስት ነጥቦች መራቅ ችሏል።
በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርስቲ ስታድየም ከአስራ ሶስት ጨዋታዎች በኋላ የተረታው ኢትዮጵያ ቡና ሊጉ ወደ አዳማ ካቀና በኋላ ያላስደፈረው መረቡ ዛሬ ግብ አስተናግዶ ለመሸነፍ ተገዷል።
በ16ኛ ስምንት መርሐግብር ኢትዮጵያ ቡና ባህርዳር ከተማን ሲገጥም ኢትዮጵያ መድኅን በበኩሉ ከሀድያ ሆሳዕና ይጫወታል
ከዚህ ጨዋታ ቀደም ብሎ በተደረገው የዕለቱ ቀዳሚ መርሐግብር መቀሌ 70 እንደርታ በከተማው የሚጫወተውን አዳማ ከተማን 2 – 0 ረቷል።
በጨዋታው አራተኛ ደቂቃ ላይ በመጀመሪያ ሳምንታት በተከታታይ ጨዋታዎች ግብ በማስቆጠር ላይ የነበረው ያሬድ ብርሀኑ ከግብ ጋር ታርቆ ቡድኑን መሪ አድርጓል።
ተጫዋቹ ረጅም ሜትሮችን እየገፋ የሄደውን ኳስ በሳጥኑ የግራ አቅጣጫ ይዞ በመግባት እና በግራ እግሩ በመምታት ኳስ እና መረብን አገናኝቷል።
የሁለተኛው አጋማሽ በተጀመረ 87ኛው ሰከንድ ላይ ደግሞ የዳንኤል ፀሐዬው ቡድን ዳግም መሪ የሆነበትን ግብ ከመረብ አሳርፏል።
በቡድኑ ሁለተኛ ጨዋታውን ያደረገው ሔኖክ አዱኛ ከቆመ ኳስ ወደ ግብ ክልል ያሻገረውን ኳስ ቤንጃሚን ኮቴ በግንባር በመግጨት ኳስ እና መረብን አዋህዷል።
ውጤቱንም ተከትሎ መቀሌ 70 እንደርታ ነጥቡን 21 በማድረስ በጊዜያዊነት 7ኛ ደረጃ ላይ የተቀመጠ ሲሆን አዳማ ከተማ በበኩሉ ሽንፈቱን ተከትሎ 15ኛ ደረጃ ላይ በመቀመጥ የወራጅ ቀጠናውን ተቀላቅሏል።
በቀጣይ ሳምንት መርሐግብር መቀሌ 70 እንደርታ ከአርባምንጭ ከተማ እንዲሁም አዳማ ከተማ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ይጫወታሉ።


