በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ15ኛ ሳምንት ጨዋታዎች በጥምቀት ዋዜማ በዕለተ ከተራ መደረግ ጀምረዋል።
በሳምንቱ ቀዳሚ ጨዋታ የፋሲል ተካልኙ ቅዱስ ጊዮርጊስ በአ.ሳ.ቴ.ዩ ስታድየም ያለውን የማሸነፍ ግስጋሴ ያስቀጠለበትን ድል በድሬዳዋ ከተማ ላይ ተቀዳጅቷል።
2 – 0 በሆነ ውጤት በተጠናቀቀው ጨዋታ የድሬዳዋ ከተማው አብዱል ጋንዩ በራሱ መረብ ላይ እንዲሁም ፍፁም ጥላሁን ከዕረፍት መልስ የፈረሰኞቹን ግብ ከመረብ አሳርፈዋል።
የቅዱስ ጊዮርጊስ ድል በሁለቱ ክለቦች የእርስ በርስ ግንኙነት ከሶስት ጨዋታዎች በኋላ የተመዘገበ ነው።
- ማሰታውቂያ -
ፍፁም ጥላሁን የውድድር ዓመቱን 6ኛ የሊግ ግብ በማስቆጠር የከፍተኛ ግብ አስቀጣሪነቱን በጥምር የሚመሩትን ተጫዋቾች መቀላቀል ችሏል።
ባለፉት ሁለት አመታት በባህርዳር ከተማ ቆይታ የነበረው ፍፁም በሁለቱ የውድድር ዘመናት በድምር ያስቆጠራቸውን የግብ ብዛቶች ለመስተካከል ሁለት ግብ ብቻ ቀርቶታል።
ተከታታይ አራተኛ ጨዋታውን በአ.ሳ.ቴ.ዩ ስታድየም ያሸነፈው ቅዱስ ጊዮርጊስ ከመሪው መቻል ጋር በአንድ ነጥብ ርቀት ብቻ ተቀምጧል።
በዚህ ስታድየም ምንም ሽንፈት ያላስተናገደው የሊጉ የ16 ጊዜ ሻምፒዮን በ33ኛ ጨዋታው ያስተናገደው 24ኛ ድሉ ሆኗል።
የይታገሱ እንዳለው ድሬዳዋ ከተማ በበኩሉ ተከታታይ አምስተኛ ድል አልባ ጉዞው የቀጠለበትን ሽንፈት አስተናግዷል።
ቡድኑ ባለፉት አራት ተከታታይ የሊጉ ጨዋታዎች ላይ የአቻ ውጤት ያስመዘገበ ሲሆን ሽንፈቱም ከ73 ቀናት በኋላ የተመዘገበ ነው።
በተለይም መሐመድኑር ናስርን ካጣ በኋላ በፊት መስመር እየተቸገረ ያለው ድሬዳዋ ከተማ አጥቂውን በጉዳት ካጣ በኋላ ባደረጋቸው አምስት ጨዋታዎች አንድ ግብ ብቻ አስቆጥሯል።
በ16ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ቅዱስ ጊዮርጊስ ሀዋሳ ከተማን ሲገጥም ድሬዳዋ ከተማ አራፊ ቡድን ነው።
በዕለቱ ሁለተኛ መርሐግብር ስሁል ሽረ ከአርባምንጭ ከተማ ተገናኝተው አዞዎቹ 1 – 0 ረተዋል።
ለበረከት ደሙው ቡድን ቡታቃ ሸመና በ73ኛ ደቂቃ ላይ ብቸኛውን ግብ ከመረብ አሳርፏል። ቡድኑ ባሳለፍነው ሳምንትም አዳማ ከተማን 2 – 0 አሸንፎ እንደነበር አይዘነጋም።
ስሁል ሽረ በበኩሉ ድሬዳዋ ላይ መቀሌ 70 እንደርታን ከረታበት ጨዋታ በኋላ በአ.ሳ.ቴ.ዩ ስታድየም ተከታታይ አራተኛ ሽንፈቱን አስተናግዷል።
በቀጣይ ሳምንት መርሐግብር አርባምንጭ ከተማ ከወላይታ ድቻ እንዲሁም ስሁል ሽረ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ይጫወታሉ።


