የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የሰባተኛ ሳምንት ጨዋታዎች በዛሬው ዕለት መደረግ ሲጀምሩ ባህርዳር ከተማ እና ወላይታ ድቻ ያለ ግብ ሲለያዩ ቅዱስ ጊዮርጊስ አርባምንጭ ከተማን አሸንፏል።
በዕለቱ ቀዳሚ ጨዋታ ከቀን 10:00 ጀምሮ የተገናኙት ባህርዳር ከተማ እና ወላይታ ድቻ ጨዋታቸውን ያለ ግብ አጠናቀዋል።
ከአሸናፊነት መልስ ወደ እዚህ ጨዋታ የመጡት ሁለቱ ቡድኖች ተከታታይ ድል ለማስመዝገብ ያደረጉት ጥረት ሳይሳካ ቀርቷል።
በጨዋታው የጣና ሞገዶቹ በይበልጥ በኳስ ቁጥጥሩ ተሽለው ዕድሎችን ለመፍጠር ሲጥሩ የጦና ንቦቹ በበኩላቸው በአጭር ቅብብሎች እና ረጃጅም ኳሶች ወደ ፊት ለመድረስ ሞክረዋል።
- ማሰታውቂያ -

ውጤቱን ተከትሎም ወላይታ ድቻ ከሶስት አመታት በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ ተከታታይ አራት የሊጉ ጨዋታዎችን ሳይሸነፍ መጓዝ ችሏል።
በስምንተኛ ሳምንት ጨዋታዎች ባህርዳር ከተማ ከስሁል ሽረ እንዲሁም ወላይታ ድቻ ከፋሲል ከነማ ይጫወታሉ።
በዕለቱ ሁለተኛ ጨዋታ ቅዱስ ጊዮርጊስ በአማኑኤል ኤርቦ የ83ኛ ደቂቃ ብቸኛ ግብ አርባምንጭ ከተማን 1 – 0 አሸንፏል።
በጨዋታው ፈረሰኞቹ የግብ ዕድሎችን በመፍጠር የተሻሉ የነበሩ ቢሆንም ግብ ለማስቆጠር ግን እስከ 83ኛው ደቂቃ ለመጠበቅ ተገደዋል።
ውጤቱን ተከትሎ ቅዱስ ጊዮርጊስ ነጥቡን 10 ሲያደርስ አርባምንጭ ከተማ በበኩሉ በነበረው 7 ነጥብ ለመቆየት ተገዷል።
በስምንተኛው ሳምንት ጨዋታዎች ቅዱስ ጊዮርጊስ ከሲዳማ ቡና እንዲሁም አርባምንጭ ከተማ ከወልዋሎ አዲግራት ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።


