በሊጉ የሳምንቱ የሁለተኛ ቀን መርሀግብር ሀዋሳ ከተማ ወደ ሊጉ መሪ የሚጠጋበትን ዕድል ሳይጠቀም ሲቀር ወላይታ ድቻ እና ሀድያ ሆሳዕና አሸናፊ ሲሆኑ የነገሌ እና መድን ጨዋታ ነጥብ በመጋራት ተጠናቋል።

ሀዋሳ ስታዲየም ላይ የነበሩ ሁለት ጨዋታዎች በተመሳሳይ የጎል መጠን በመሸናነፍ የተጠናቀቁ ናቸው። ቀደም ሲል ዘጠኝ ሰዓት ላይ ወደ መሪው ለመጠጋት ለሀዋሳ ከተማ ወሳኝ በነበረ ጨዋታ በፋሲል ከነማ ሽንፈትን ለማስተናገድ ተገደዋል። እጅግ በከባድ ዝናብ ታጅቦ በተደረገው የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ በማይመች የሜዳ አቅርቦት ጥሩ ፉክክርን ያሳዩበት በንፅፅር ሀዋሳ ከተማዎች በኳስ ቁጥጥሩ ሻል ቢሉም በረጃጅም ኳሶች ሲጫወት የሚታዩት ፋሲል ከነማዎች ግን አሸናፊ መሆን የቻሉበት ነበር። 67ኛው ደቂቃ ላይ ወደ ቀኝ ካደላ ቦታ የተገኘውን የቅጣት ምት ወጣቱ ኪሩቤል ዳኜ በረጅሙ ወደ ግብ ክልል ሲያሻማ የሀዋሳ ተከላካዮች የአቋቋም ስህተት ታክሎበት ምኞት ደበበ በግንባር ጨረፍ በማድረግ የዳግም ተፈራ መረብ ላይ ያሳረፋት ኳስ አፄዎቹን 1ለ0 አሸናፊ ማድረግ የቻለች ግብ ሆናለች።

ምሽቱን እጅግ ጠንካራ ፉክክርን ፋታ በማይሰጠው የሳጥን ሳጥን ሩጫ ደምቆ መታየት በቻለው የወልዋሎ ዓዲግራት ዩኒቨርስቲ እና ወላይታ ድቻ ጨዋታ በመጨረሻዎቹ የጭማሪ አራት ደቂቃዎች ውስጥ የጨዋታው ብቸኛ ጎል መገኘት ችላለች። 90+1ኛው ደቂቃ ላይ ተቀይሮ የገባው ቴዎድሮስ ታፈሠ በግሩም እይታ የተቆጣጠራትን ኳስ በአግባቡ አሾልኮ ሰጥቶት ሌላኛው ተቀይሮ የገባው መሳይ ሠለሞን በአስደናቂ አጨራረስ ወጋ በማድረግ ያስቆጠራት ጎል በመጨረሻም የጦና ንቦቹ 1ለ0 አሸንፈው ጣፋጭ ሦስት ነጥብን እንዲያገኙ ሆኗል።

በአዲስ አበባው አበበ ቢቂላ ስታዲየም ላይ ነገሌ አርሲን ከ ኢትዮጵያ መድን ያገናኘው ጨዋታ 1ለ1 መቋጫውን አድርጓል። ጥሩ አጀማመርን ያደረጉት ነገሌ አርሲዎች ጎል እና መረብን 22ኛው ደቂቃ ላይ ከመረብ አዋህደዋል። ከሀቢብ ከማል ያገኛትን ኳስ ኪቲካ ጀማ ወደ ሳጥን ይዞ ገብቶ አቡበከር ኑራ መረብ ላይ በማስቀመጥ ቡድኑን ቀዳሚ ቢያደርግም በሁለተኛው አጋማሽ ብሎጫውን ይዘው ሜዳ ላይ የተቀረቡት ኢትዮጵያ መድኖች ጥረታቸው ተሳክቶ የአቻነት ጎል አግኝተዋል። 80ኛው ደቂቃ ላይ የአማኑኤል ኤርቦ ድንቅ የማቀበል ጥበብን ብሩክ በላቸው በጥሩ አጨራረስ አስቆጥሮ በመጨረሻም ጨዋታው 1ለ1 በሆነ የአቻ ውጤት ተቋጭቷል።

አርባምንጭ ከተማ ወደ ላይ ከፍ የሚልበትን ዕድል በሀድያ ሆሳዕና ተሽንፎ መጠቀም ሳይችል ቀርቷል። 10ኛው ደቂቃ ላይ ተመስገን ብርሀኑ ወደ ቀኝ የሳጥኑ ክፍል የተሰነጠቀለትን ኳስ ወደ ይዞ ለመግባት ጥረት ሲያደርግ አካሉ አትሞ በሰራበት ጥፋት የዕለቱ ኢንተርናሽናል ዳኛ ማኑሄ ወልደፃዲቅ የሰጡትን የፍፁም ቅጣት ምት አምበሉ ሔኖክ አርፊጮ ጎል አድርጓታል። ቀጣዮቹን ደቂቃዎች አዞዎቹ የበላይ ሆነው ቢታዩም በ1ለ0 ሽንፈት ለማጠናቀቅ ተገደዋል።

አስተያየት ይስጡ