በሀገሪቱ እግር ኳስ ትልቅ ቦታ የሚሰጠው የሸገር ደርቢ ኢትዮጵያ ቡና 3ለ1 በሆነ ውጤት ቅዱስ ጊዮርጊስን ማሸነፍ ችለዋል።

እጅግ በርካታ ደጋፊዎች ስታዲየሙን በሞሉበት እና የቀድሞው የሁለቱ ክለብ ተጫዋቾች የወዳጅነት ጨዋታን ካደረጉ በኋላ በኢንተርናሽናል ዋና ዳኛ ዳንኤል ይታገሱ በተመራው ጨዋታ በመጀመሪያው አጋማሽ ሁለት ጎሎችን ያስመለከተን ነበር። 24ኛው ደቂቃ ላይ ከግራ መስመር ሔኖክ ዮሐንስ ወደ ሳጥን ያሻማውን ኳስ ሀብታሙ ጉልላት ተቆጣጥሮ የቡናማዎቹ ተከላካዮች ስህተት ታክሎበት ፍፁም ጥላሁን አራተኛ ተከታታይ ጎሉን በማስቆጠር ፈረሰኞቹን ቀዳሚ አድርጓል። ጨዋታው ቀጥሎ አጋማሹ በዚህ ውጤት ይገባደዳል ተብሎ ሲጠበቅ በተሰጠው ጭማሪ ደቂቃ 45+3 ላይ ከግራ ሳጥን መስመሩ ጠርዝ ላይ አምበሉ ራምኬል ጀምስ የሰጠውን ኳስ የያአብስራ ጎሳዬ ስህተት ታክሎበት ኦካይ ጁል ቡናማዎቹን 1ለ1 ማድረግ የቻለች ጎል መረቡ ላይ አሳርፏል።

ብዙም የጨዋታ ግለቱ ከፍ አይበል እንጂ በደጋፊዎች ህብረ ዝማሬ ደምቆ ቡናማዎቹን መጠነኛ ማነቃቃት ውስጥ ከቶ የተመለሰው ሁለተኛው አጋማሽ 53ኛው ደቂቃ ፉአድ ኢብራሂም ከራሱ ሜዳ በረጀሰሙ የላካትን ኳስ ናይጄሪያዊው አጥቂ አቡበከር አዳሙ ከብሩክ ታረቀኝ ጋር ታግሎ ወደ ኋላ በግንባር ጨርፎ የሰጠውን ኳስ ቢኒያም ጌታቸው በቀላሉ ኢትዮጵያ ቡናን መሪ ያደረገች ጎል ሲያስቆጥር 66ኛው ደቂቃ ላይ ደግሞ ዲቫይን ዋቹኩዋ ከማዕዘን አሻምቶ በንክኪ ኳስን ያገኘው ዘላለም አባተ ተጨማሪ ጎል በማከል ጨዋታው በመጨረሻም በኢትዮጵያ ቡና 3ለ1 አሸናፊነት ተቋጭቷል።

አስተያየት ይስጡ