በሊጉ የሳምንቱ የመጀመሪያ ቀን ጨዋታ ኢትዮጵያ መድን ቅዱስ ጊዮርጊስን 3ለ0 አሸንፏል።
በጨዋታ የመጀመሪያዎቹ አስር ደቂቃዎች ብልጫውን የወሰዱት መድኖች የፈረሰኞቹ ተከላካይ ብሩክ ታረቀኝ የተሳሳተውን ኳስ ብሩክ ሙሉጌታ ከማይመች ቦታ ላይ ሆኖ ሞክሮ ለጥቂት በወጣችበት ቅፅበት ፈጣን ሙከራን ሰንዝረዋል። በቀጣዮቹ ደቂቃዎች በተሻለ ፈጣን ሽግግር ለመንቀሳቀስ ጥረት ወደ ማድረጉ የገቡት ቅዱስ ጊዮርጊሶች ሁለት የሚያስቆጩ አጋጣሚዎችን አግኝተዋል። ሀብታሙ ጉልላት ከመስመር ፍፁም ጥላሁን የሰጠውን ኳስ ወደ ጎል ሞክሮ በግብ ዘቡ አቡበከር ኑራ የተመለሰችን ኳስ ፀጋ ከድር ቢያገኛትም በጨዋታው ጥሩ ጊዜን ያሳለፈው አቡበከር አሁንም አክሽፏታል።
በሌላ ሙከራም ከቅጣት ምት ሀብታሙ ነካ አድርጎ የሰጠውን ብርሀኑ አሻሞ አክርሮ መቶ አቡበከር ኑራ ሲተፋት ነፃ ሆኖ ኳስን ያገኘው ሀብታሙ ጉልላት የውጪን መረብ አስነክቶ ኳሷ ወደ ውጪ ወጥታበታለች። ጨዋታዎች ሰላሳዎቹን ደቂቃዎች ሲያጋምስ በድጋሚ ወደ ጨዋታው የገቡት መድኖች ወገኔ ገዛኸኝ አሻምቶ ረመዳን በግንባር ከገጫት ሙከራቸው በኋላ መሪ የሆኑበትን ጎል አስቆጥረዋል። 41ኛው ደቂቃ ላይ ከቀኝ መስመር ረመዳን አሻግሮ ወጣቱ አማካይ ዳዊት በላቸው በደረት አብርዶ የሰጠውን ወገኔ እንድምንም ወደ ቀኝ ላዘነበለው ብሩክ ሙሉጌታ አቀብሎት አጥቂው ሳይቸገር አስቆጥሮታል
ከዕረፍት መልስ በቀጠለው ጨዋታ ጠንከር ያለውን ሙከራ ያስተዋልነው 60ኛው ደቂቃ ላይ ነበር። ከቀኝ መስመር እጅ ውርወራ ተነስታ ከጥሩ ቅብብል በኋላ ፍፁም ጥላሁን ከግራ በኩል ያገኘውን ኳስ አሻምቶ ተገኑ ተሾመ በግንባር ገጭቶ አቡበከር ኑራ በግሩም ቅልጥፍና ኳሷን ከጎልነት ታድጓታል።
- ማሰታውቂያ -
በቀጣዮቹ ደቂቃዎች አንዳች ነገርን ለመፍጠር የተንቀሳቀሱት መድኖች 61ኛው ደቂቃ ላይ ረመዳን የሱፍ ከተከላካይ ጀርባ የጣለውን ኳስ ከጨዋታ ውጪ በሚል የተዘናጉት የቅዱስ ጊዮርጊስ ተከላካዮች አምልጦ ብሩክ ሙሉጌታ ግብ ጠባቂው ፋሩክን አልፎ ለራሱም ለቡድኑ ሁለተኛ ጎል አድርጓታል። 88ኛው ደቂቃ ላይ አሚኑ ነስሩ በሰራው ስህተት ብሩክ በላቸው ያገኛትን ኳስ ፋሩክ ሻኪሉን በማለፍ ተጨማሪ ጎል አክሎ ጨዋታው 3ለ0 መድንን ከአምስት ጨዋታዎች በኋላ ባለ ድል አድርጓል።


