በሳምንቱ የመክፈቻ ቀን የተደረጉ የአዳማ ጨዋታዎች ወላይታ ድቻ ከአርባምንጭ 0ለ0 ቅዱስ ጊዮርጊስ ከ መቐለ 1ለ1 በሆኑ የአቻ ውጤቶች ተቋጭተዋል።
ወላይታ ድቻ 0-0 አርባምንጭ ከተማ
ሁለቱን ጎረቤታም ክለቦችን ያገናኘው የአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርስቲ ስታዲየም የሳምንቱ የመክፈቻ ጨዋታ በመጀመሪያው አጋማሽ በተወሰነ መልኩ ወደ መስመር በማድላት ወላይታ ድቻዎች የተሻሉ ቢመስሉም አጋማሹ በይበልጥ ግን በመከላከል የተጠመደ ነበር። ከነበረው የማጥቃት ደመ ነብስ መቀዛቀዝ አኳያ የጦና ንቦቹ 40ኛው ደቂቃ ላይ ኪዳኔ አሰፋ ያቀበለውን ኳስ ዮናታን ኤልያስ ከሳጥን ውጪ አክርሮ መቶ ቶጓዊው የግብ ዘብ ኢድሪሳ ኦጎዶጆ በጥሩ ብቃት ካወጣት አጋጣሚ በስተቀር ሙከራዎችን ሳንመለከት ወደ መልበሻ ክፍል ጨዋታው አምርቷል።
ከዕረፍት መልስ ከቆመበት የቀጠለው የቡድኖቹ እንቅስቃሴ ጥራች ባላቸው ሙከራዎች መድመቅ የተሳነው ነበር። 83ኛው ደቂቃ ላይ ወላይታ ድቻዎች ቴዎድሮስ ታፈሠ ከቅጣት አሻምቶ አካሉ አትሞ በግንባር ገጭቶ በራሱ መረብ ላይ ለማሳረፍ የሞከራትን ኳስ ቶጓዊው የግብ ዘብ ኢድሪሳ በሚገርም ቅልጥፍና አርባምንጭን ታድጎ በመጨረሻም ጨዋታው እንደነበረው መቀዛቀዝ የሚገባውን ውጤት ይዞ 0ለ0 ተፈፅሟል።
- ማሰታውቂያ -
መቐለ 70 እንደርታ 1-1 ቅዱስ ጊዮርጊስ
ተመጣጣኝ የሚመስል የሜዳ ላይ የኳስ ንክኪዎች በነበሩት የመጀመሪያው አጋማሽ የመጨረሻው ሜዳ ላይ መቐለዎች በይበልጥ ብልጫውን ለመውሰድ የሚያሳዩት ጥረት የገዘፈ ቢመስልም የሚያገኟቸውን ዕድሎች ግን መጠቀሙ ላይ ተዳክመው ታይተዋል። ፍፁም ከቅጣት ምት ሞክሮ የግብ ዘቡ ተመስገን ዮሐንስ የመለሳት በድጋሚ በጥሩ ቅብብል አሸናፊ ለኪቲካ ሰጥቶት አጥቂው ያለቀለት ዕድል ለፍፁም ሲሰጠው ተጫዋቹ ወደ ጎል ቢሞክርም አሁንም ተመስገን ያዳናት አጋጣሚ የምትጠቀሰዋ ሌላኛዋ ሙከራቸው ነበረች።
በሽግግር በመጫወት አንዳች ነገርን ለመፍጠር ከአራት ጨዋታዎች በኋላ ከጉዳት በተመለሰው አቤል ያለው አማካኝነት ጥቃት ሲሰነዝሩ የታዩት ፈረሰኞቹ አቤል ያለው የግብ ዘቡ መሐመድ ዜጉን መውጣት አይቶ ወደ ጎል ያደረጋት ሙከራ ለጥቂት ከወጣች በኋላ ጨዋታው 40ኛው ደቂቃ ላይ ሲደርስ ብርሀኑ አሻሞ ወደ ግራ የጣለውን ኳስ ተገኑ ተሾመ ወደ ውስጥ ሰብሮ ገብቶ ያቀበለውን አቤል ያለው ጎል በማድረግ ቡድኑን ቀዳሚ አድርጓል።

ከዕረፍት መልስ በቀጠለው የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ መቐለዎች የተሻለውን ቆይታ ማድረግ ሲችሉ ፈረሰኞቹ በመከላከል ላይ በተወሰነ መልኩ አተኩረው የታዩበት ነበር። በሞዓም አናብስቱ በኩል ኪቲካ ከቀኝ ያገኘውን ኳስ መጠቀም ያልቻለበት እና አቤል ለቅዱስ ጊዮርጊስ ሁለተኛ ጎል የምትሆን አጋጣሚን አግኝቶ የግብ ዘቡ መሐመድ ዜጉ ያመከነበት ዕድሎች ይጠቀሳሉ። ጨዋታው 80ኛው ደቂቃ ላይ ሲደርስ ከማዕዘን የተነሳችን ኳስን አሸናፊ በግንባር ጨርፎ ተመስገን ያገኛትን ኳስ በቀጥታ ወደ ጎል መቶ መቐለን አቻ ሲያደርግ ከጎሏ መቆጠር በኋላ ተቀይሮ የወጣው አቤል ያለው ተጠባባቂ ወንበር ላይ ከቡድን አጋሮቹ ጋር ግጭት ውስጥ የገባበት ክስተት መነጋገሪያ ሆኖ በመጨረሻም ጨዋታው 1ለ1 ተጠናቋል።


