ሀዋሳ ከተማ ሲያሸንፍ ቅዱስ ጊዮርጊስ ከ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በአቻ ውጤት አጠናቀዋል።
ሸገር ከተማ 1-2 ሀዋሳ ከተማ
በኢንተርናሽናል ዋና ዳኛ ቴዎድሮስ ምትኩ መሪነት የጀመረው የአዳማ ዩኒቨርስቲ ስታዲየም ቀዳሚው መርሀግብር ኳስን በይበልጥ ይዞ በመንቀሳቀስ የተሻሉ የነበሩት ሀዋሳ ከተማዎች ቢሆኑም የመጨረሻው የሜዳ ክፍል ላይ የነበራቸው ልልነት ግን እጅግ ቀዝቃዛ ነበር። በተጋጣሚያቸው የኳስ ቁጥጥሩን ቢበለጡም በሽግግር ተንቀሳቅሰው ጎልን ለማስቆጠር ጥረት ያደረጉት ሸገር ከተማዎች 27ኛው ደቂቃ ላይ ከቀኝ የሜዳው ክፍል አሚር አብዶ ወደ ሳጥን ጠርዝ ያሻገራትን ኳስ ናትናኤል ዘለቀ ሙከራ በሚያደርግበት ወቅት አንተነህ ተፈራ ደርሶት በቀጥታ ወደ ግብ ሲመታ ተከላካዩ ወንድማገኝ ማዕረግ በመንካቱ ኳሷን እግሩ ስር ያገኘው ያሬድ መኮንን በቀላሉ አዲስ አዳጊውን መሪ ያደረገ ጎል ከመረብ አሳርፏል።
ከዕረፍት ጨዋታው ሲመለስ ይበልጡኑ ወደ ሳጥን በተጠጋ እንቅስቃሴዎች ብልጫውን መውሰድ የቻሉት ሀዋሳዎች ከቀኝ በጥልቀት ቢኒያም በላይ ወደ መሐል በማስገባት በሽመልስ ፣ ያሬድ ፣ ጌታነህ እና ቢኒያም ንክኪዎች በመታገዝ ጫናን ማሳደር ችለዋል። ሽመልስ ካመከናት ግልፅ አጋጣሚ በኋላ 62ኛው ደቂቃ ላይ ብሩክ ታደለ ከማዕዘን ያሻማትን ኳስ ቾል ላም በግንባር ገጭቶ ከራሱ የግብ ክልል ለማራቅ ጥረት ሲያደርግ ሳጥኑ ጫፍ የተገኘው ታዳጊው ብሩክ ያሬድ በዚህ አመት ሦስኛዋን አሰደናቂ ጎል በግምት ከሀያ ሜትር ርቀት ባህሩ ነጋሽ መረብ ላይ አሳርፎ ሀዋሳን አቻ አድርጓል። ጨዋታው ቀጥሎ 69ኛው ደቂቃ ላይ ቢኒያም በላይ በረጅሙ የሰጠውን ኳስ ሽመልስ ሳጥን ውስጥ አግኝቶ ሲሞክር የግብ ዘቡ ባህሩ ነጋሽ ሲመለስ የተመሰችዋን ኳስ ያገኘው ጌታነህ ከበደ መረብ ላይ አሳርፎ ጨዋታው በቀሩ ደቂቃዎች ጎል ሳይቆጠር በሀዋሳ የበላይነት 2ለ1 ተቋጭቷል
- ማሰታውቂያ -
ቅዱስ ጊዮርጊስ 1-1 ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ
በጥሩ እንቅስቃሴ ሀያ ደቂቃዎችን በተሻለ መንቀሳቀስ ቢችሉም ቀስ በቀስ ግን ተጋጣሚያቸው ንግድ ባንክ ወደ ጨዋታ ቅኝት ውስጥ ቢገቡም ቶሎ ቶሎ ከማጥቃት እንቅስቃሴ ያልቦዘኑት ቅዱስ ጊዮርጊሶች እንደነበራቸው ብልጫ 33ኛው ደቂቃ ላይ ጎል አስቆጥረዋል። ፀጋ ከድር ከቀኝ መስመር ወደ ውስጥ የጣለውን ኳስ የአብስራ አመቻችቶ ሲሰጠው ሀብታሙ ጉልላት ወደ ጎልነት ለውጦ ፈረሰኞቹን ቀዳሚ አድርጓል። ፊልሞን ገብረፃዲቅ ካደረጋት ብቻ ሙከራ በስተቀር በተጋጣሚያቸው አንፃራዊ ብልጫን የወሰደባቸው ንግድ ባንኮች በ1ለ0 የቅዱስ ጊዮርጊስ መሪነት ወደ መልበሻ ክፍል ጨዋታው አምርቷል
ከዕረፍት መልስ በቀጠለው የምሽቱ መርሀግብር በእንቅስቃሴ አሁንም ፈረሰኞቹ ሻል ያለውን ጊዜ ቢወስዱም በተቃራኒው ንግድ ባንኮች የተጫዋችን ስህተት ተጠቅመው አቻ የሆኑበት ነበር። 75ኛው ደቂቃ ላይ ብሩክ ብፁአምላክ ወደ ግራ ካደላ ቦታ በረጅሙ ወደ ሳጥን የጣላትን ኳስ የኬኒያዊው የፈረሰኞቹ ግብ ጠባቂ ፋሩክ ሸኪሎ ስህተት ታክሎበት ናትናኤል ዳንኤል በግንባር ገጭቶ በማስቆጠር ጨዋታው 1ለ1 በሆነ የአቻ ውጤት ተጠናቋል።


