ሲዳማ ቡና እና ድሬዳዋ ከተማ በተመሳሳይ 2ለ1 በሆነ ውጤት ተጋጣሚዎቻቸውን ረተዋል።
ምድረገነት ሽረ 1-2 ሲዳማ ቡና
ሲዳማ ቡናዎች ጥሩ አጀማመር ባደረጉበት የመጀመሪያዎቹ አስር ደቂቃዎች በተመስገን በጅሮንድ ያለቀለት ሙከራን ቢያደርጉም ጎል ያስተናገዱት ግን በጉዜ ነበር። 11ኛው ደቂቃ ሽመክት ጉግሳ የግል ጥረት ተጠቅሞ የሰጠውን ኳስ አቤል ማሙሽ በጥሩ አጨራረስ መረብ ላይ አሳርፎ ምድረገነት ሽረን መሪ አድረጓል። ጎል ካስቆጠሩ በኋላ በይበልጥ ከተጋጣሚያቸው በብዙ መልኩ የተሻሉ የነበሩት ሽረዎች በአቤል ማሙሽ እና ዳንኤል ዳርጌ አማካኝነት በድግግሞሽ የመጨረሻው ሜዳ ላይ ጥራት ያላቸውን ኳሶች ቢያገኙም ተጨማሪ ጎል ማድረጉ ላይ ግን እጅግ ደካሞች ሆነው ታይተዋል።
ከዕረፍት መልስ በተሻለ ተነሳሽነት በሽግግር መጫወትን መርጠው የተመለሱት ሲዳማ ቡናዎች ብለስ ናጎ ባደረጋት አደገኛ ክፍሎም ገብረህይወት ከግቡ መስመር ላይ ባወጣት አደገኛ ሙከራ ወደ ተጋጣሚያቸው ሦስተኛ የሜዳ ክፍል ላይ በቀጣዮቹ ደቂቃዎች ቶሎ ቶሎ ሲደርሱ ያስተዋልን ሲሆን 62ኛው ደቂቃ ላይ የአቻነት ጎልን አግኝተዋል። አስቻለው ሙሴ ያሻገረውን ኳስ ፍቅረየሱስ ተወልደብርሃን በግንባር ገጭቶ ከመረብ ሲያሳርፍ ከሦስት ደቂቃዎች በኋላ ደግሞ ምድረገነት ሽረዎች በቀይ ተጫዋቾቻቸውን ለማጣት ተገደዋል።
- ማሰታውቂያ -


ክፍሎም ገብረህይወት በሰራው ጥፋት ቢጫ ካርድ ማየቱን ተከትሎ ከዕለቱ ዳኛ ዳንኤል ግርማይ ጋር ያልተገባ ሰጣገባ ውስጥ በመግባቱ በሁለት ቢጫ በቀይ ካርድ ከሜዳ ሊወገድ ችሏል። አሸናፊ ሆኖ ለመውጣት ጫና ማሳደራቸውን አጠናክረው የቀጠሉት ሲዳማ ቡናዎች 81ኛው ደቂቃ ከመስመር የተሻማን ኳስ ብርሀኑ በቀለ በግንባር ገጭቶ በማስቆጠር በመጨረሻ ሲዳማ ቡና 2ለ1 አሸንፎ ወጥቷል።
ድሬዳዋ ከተማ 2-1 ወልዋሎ አዲግራት ዩ
በዋና ዳኛው ኤፍሬም ደበሌ መሪነት የጀመረው የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ በመጀመሪያው አጋማሽ ተመጣጣኝ ፉክክር የታየበት ቢመስልም የቡድኖቹ የማጥቃት ደመ ነብስ ግን በእጅጉ የተደከመ መልክን ቢላበስም በአጋማሹ ከቆመ ኳስ ጎልን ድሬዳዋ ከተማዎች አስቆጥረዋል። 37ኛው ደቂቃ ከማዕዘን ምት አቤል አሰበ ሲያሻማ ያሬድ ታደሰ በግንባር ገጭቶ በማስቆጠር የምስራቁን ክለቡ ቀዳሚ ማድረግ ችሏል።

ከዕረፍት መልስ ተሻሽለው የቀረቡት እና ደጋግመው ማጥቃት ላይ ትኩረት ባደረገ እንቅስቃሴ መጫወት ሲችሉ የነበሩት ወልዋሎች እንደነበራቸው የጨዋታ ብልጫ ጎል ማስቆጠር ባለመቻላቸው ሁለተኛ ጎልን ለማስተናገድ ተገደዋል። 67ኛው ከግራ የተነሳች ኳስን አብዱሰላም የሱፍ በጥልቀት እየነዳ ገብቶ መረብ ላይ በማሳረፍ የቡድኑን የጎል መጠን ወደ ሁለት ከፍ አድርጓል። አጋማሹን በተሻለ ንቃት ቢጀምሩም ጎልን ማስተናገዳቸው ግድ የሆነባቸው ቢጫዎቹ 82ኛው ደቂቃ በዳዊት ገብሩ ጎል ቢያክሉም ከመሸነፍ ሳይድኑ ጨዋታው 2ለ1 በሆነ ውጤት በድሬዳዋ አሸናፊነት ተቋጭቷል።


