የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ31ኛ ሳምንት ጨዋታዎች በዛሬው ዕለት በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርስቲ ስታድየም መደረግ ጀምረዋል።
የዕለቱ እንዲሁም የሳምንቱ ተጠባቂ በነበረው ጨዋታ የሊጉ መሪ ከተከታዩ ያለው የነጥብ ልዩነት የጠበበበት ውጤት ተመዝግቧል።
ከአመሻሽ 12:00 ጀምሮ በተደረገው ጨዋታ ላይ በርከት ባሉ ደጋፊዎቻቸው ታጅበው መሪው ኢትዮጵያ መድንን የገጠሙት ቡናማዎቹ 1 ለ 0 አሸንፈዋል።

- ማሰታውቂያ -
በ43ኛው ደቂቃ ላይ ዲቫይን ዋቹኩዋ ከማዕዘን ያሻገረውን ኳስ ተጠቅሞ አምበሉ ራምኬል ጀምስ ያስቆጠረው ግብ ኢትዮጵያ ቡናን አሸናፊ ለማድረግ በቂ ሆኗል።
የነፃነት ክብሬው ቡድን ድሉን ተከትሎ ነጥቡን 54 በማድረስ ከመሪው እና ከዛሬ ተጋጣሚው ኢትዮጵያ መድን ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ ስድስት አጥብቧል።
ቡድኑ የዛሬውን ጨዋታ ጨምሮ ያለፉትን አምስት ተከታታይ ጨዋታዎች ምንም ግብ ሳያስተናግድ አሸንፏል።
በውድድር ዓመቱ አምስተኛ የሊግ ሽንፈትን ያስተናገደው ኢትዮጵያ መድን በነበረው 60 ነጥብ በመሪነት ቀጥሏል።
በቀጣይ ቀሪ ጨዋታዎች ኢትዮጵያ መድን ከሲዳማ ቡና ፣ ከቅዱስ ጊዮርጊስ ፣ ከመቻል ፣ ከሀድያ ሆሳዕና እና ከስሁል ሽረ ይጫወታል።
ኢትዮጵያ ቡና በበኩሉ ከወልዋሎ አዲግራት ፣ አርባምንጭ ከተማ ፣ መቀሌ 70 እንደርታ ፣ ቅዱስ ጊዮርጊስ እና ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ይጫወታል።
በዕለቱ አስቀድሞ በከ9:00 ጀምሮ በተደረገው ጨዋታ ደግሞ አርባምንጭ ከተማ መውረዱን ካረጋገጠው ወልዋሎ አዲግራት ጋር አቻ ተለያይቷል።
በጨዋታው ናትናኤል ሰለሞን ለወልዋሎ አዲግራት ታምራት ኢያሱ ደግሞ ለአርባምንጭ ከተማ ኳስ እና መረብን ያገናኙ ተጫዋቾች ናቸው።


