የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ26ኛ ሳምንት መርሐግብር በዛሬው ዕለት በተደረጉ ሁለት ጨዋታዎች ተጠናቋል።
በዕለቱ ቀዳሚ ጨዋታ ኢትዮጵያ መድን ኢትዮ ኤሌክትሪክን በመሐመድ አበራ ግቦች 2 ለ 0 አሸንፏል።
በአበቡከር ሳኒ ላይ በተሰራው ጥፋት የተገኘውን የፍፁም ቅጣት ምት በ75ኛው ደቂቃ ላይ ያስቆጠረው መሐመድ አበራ በ86ኛው ደቂቃ ላይ ደግሞ ያሬድ ካሳዬ ያሻገረለትን ኳስ በግንባር በመግጨት ከመረብ አሳርፏል።
ውጤቱንም ተከትሎ ኢትዮጵያ መድን ነጥቡን 51 በማድረስ ከተከታዩ ባህርዳር ከተማ ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ 11 አስፍቷል።
- ማሰታውቂያ -

ኢትዮ ኤሌክትሪክ በበኩሉ በ29 ነጥቦች በነበረበት 13ኛ ደረጃ ላይ ለመቆየት ተገዷል።
በ27ኛው ሳምንት ኢትዮጵያ መድን ከአርባምንጭ ከተማ እንዲሁም ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከባህር ዳር ከተማ ይጫወታሉ።
ከአመሻሽ 12:00 ጀምሮ በተደረገው ጨዋታ ደግሞ በበርካታ ደጋፊዎቹ ፊት የተጫወተው ሀዋሳ ከተማ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክን 2 ለ 1 አሸንፏል።
ሱሌማን ሀሚድ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክን መሪ አድርጎ የነበረ ግብ በ16ኛው ደቂቃ ላይ በቀጥታ ከቅጣት ምት ከመረብ አሳርፎ ነበር።
ነገር ግን ኤርትራዊው አሊ ሱሌማን በ37ኛው እና በ80ኛው ደቂቃዎች ላይ ከብሩክ ታደለ እና ታፈሰ ሰለሞን የደረሱትን ኳሶች ተጠቅሞ ሀዋሳ ከተማን አሸናፊ ያደረጉ ግቦችን አስቆጥሯል።
ባሳለፍነው ሳምንትም ወላይታ ድቻን 1 ለ 0 አሸንፎ የነበረው ሀዋሳ ከተማ በውድድር ዓመቱ ለመጀመሪያ ጊዜ በተከታታይ ጨዋታዎች አሸንፏል።
ውጤቱንም ተከትሎ ሀዋሳ ከተማ ነጥቡን 27 በማድረስ ከወራጅ ቀጠናው ለመውጣት የሚያደርገውን ጥረት አጠናክሯል።
ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በበኩሉ በ35 ነጥቦች የ7ኛ ደረጃን ይዞ ይገኛል።
በ28ኛው ሳምንት ሀዋሳ ከተማ ከሲዳማ ቡና ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ደግሞ ከመቻል ይጫወታሉ።


