የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ26ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ሁለት ጨዋታዎች በሀዋሳ ዩኒቨርስቲ ስታድየም ተደርገዋል።
ከቀን 9:00 ጀምሮ በተደረገው ቀዳሚው ጨዋታ ሲዳማ ቡና ኢትዮጵያ ቡናን 1 ለ 0 አሸንፏል።
በጨዋታው ፍቅረየሱስ ተክለብርሃን በ13ኛው ደቂቃ ላይ ያስቆጠረው ግብ ሲዳማ ቡናን አሸናፊ ለማድረግ በቂ ነበር።
ፍቅረየሱስ ተክለብርሀን ባለፉት ሁለት ተከታታይ ጨዋታዎች ቡድኑ አርባምንጭ ከተማን እና ባህርዳር ከተማን ሲያሸንፍ የማሸነፊያ ብቸኛ ግቦቹን ማስቆጠሩ ይታወሳል።
- ማሰታውቂያ -
የዓመቱ ዘጠነኛ የሊግ ድሉን ያስመዘገበው ሲዳማ ቡና በስምንቱ ጨዋታዎች ግብ ሳይቆጠርበት አሸንፏል።
ውጤቱንም ተከትሎ ሲዳማ ቡና ነጥቡን 35 በማድረስ የዘጠነኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል።
የውድድር ዘመኑን ሰባተኛ ሽንፈት ያስተናገደው ኢትዮጵያ ቡና ከኢትዮጵያ መድን ያለውን ልዩነት የሚያጠብበትን ዕድል ዳግም ሳይጠቀም ቀርቷል።
በ27ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ኢትዮጵያ ቡና ከድሬዳዋ ከተማ ሲዳማ ቡና ደግሞ ከሀዋሳ ከተማ ጋር ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
በዕለቱ ሁለተኛ ጨዋታ ከአመሻሽ 12:00 ጀምሮ የተገናኙት አርባምንጭ ከተማ እና ስሁል ሽረ ያለ ግብ ጨዋታቸውን አጠናቀዋል።
ውጤቱንም ተከትሎ አርባምንጭ ከተማ ነጥቡን 38 በማድረስ ለጥቂት ሰዓታት ተነጥቆ ወደነበረበት ወደ 8ኛ ደረጃ ተመልሷል።
ስሁል ሽረ በበኩሉ ነጥቡን 18 ያደረሰ ሲሆን በደረጃው ላይ ግን ለውጥ ሳያደርግ በ17ኛ ደረጃ ለመቆየት ተገዷል።
በ27ኛ ሳምንት ጨዋታዎች አርባምንጭ ከተማ ከኢትዮጵያ ቡና እንዲሁም ስሁል ሽረ ከወላይታ ድቻ ይጫወታሉ።
የሊጉ መርሐግብር በነገው ዕለትም ሲቀጥል አዳማ ከተማ ከመቻል ፤ ፋሲል ከነማ ከድሬዳዋ ከተማ እንዲሁም ባህርዳር ከተማ ከመቀሌ 70 እንደርታ ይገናኛሉ።


