የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 21ኛ ሳምንት የመጨረሻ ጨዋታዎች በዕለቱ ሲደረጉ በቀዳሚው ጨዋታ መቻል እና ወልዋሎ አዲግራት ነጥብ ተጋርተዋል።
ሁለቱ ከድል የተራራቁ ክለቦችን ባገናኘው ጨዋታ የላቀ የስብስብ ጥራት የያዘው መቻል በኳስ ቁጥጥሩ እና ወደ ተጋጣሚው የግብ ክልል ከመድረስ አንፃር የተሻለ ነበር።
ነገር ግን ከፊት መስመር ላይ ኳስና መረብን የሚያገናኝለት ተጫዋች ሳያገኝ ጨዋታውን አጠናቋል።
በአሰልጣኝ ገብረክርስቶስ ቢራራ የሚመራው ቡድኑ ሊጉ የድሬደዋ ቆይታውን ሲያጠናቅቅ እና ወደ አዳማ ሲመጣ በመሪነት ላይ ተቀምጦ ነበር።
- ማሰታውቂያ -

ነገር ግን በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርስቲ ስታድየም ላይ ካደረጋቸው ዘጠኝ ተከታታይ ጨዋታዎች በአንዱ(ስሁል ሽረን) ብቻ ነው ያሸነፈው።
መቻል አዳማ ላይ ማግኘት ከሚገባው 27 ነጥቦች ማሳካት የቻለው ስምንቱን ብቻ ነው። በደረጃ ሰንጠረዡም በ29 ነጥቦች 7ኛ ላይ ሆኖ ሳምንቱን አጠናቋል።
የሊጉን ግርጌ ይዞ ለበርካታ ሳምንታት በመዝለቅ ላይ ያለው ወልዋሎ አዲግራት የውድድር ዓመቱን ስድስተኛ የአቻ ውጤት አስመዝግቧል።
ቡድኑ ባለፉት ሰባት ተከታታይ ጨዋታዎች ላይ ከአንድ በላይ ግብ የማያስተናግድ ቢሆንም በተመሳሳይ የአጥቂ ክፍሉም በጨዋታ ከአንድ በላይ ግብ ማስቆጠር አልቻለም።
ከመጀመሪያ 12 የሊጉ ጨዋታዎች በ11 ተሸንፎ የነበረው ወልዋሎ አዲግራት ካለፉት ሰባት ጨዋታዎች በአንዱ ብቻ ሽንፈት ያስተናገደው።
አሁንም ከ18ኛ ደረጃ መላቀቅ ባይችልም ነጥቡን ግን ዘጠኝ አድርሷል።
በቀጣይ ሳምንት መርሐግብር መቻል ከፋሲል ከነማ ወልዋሎ አዲግራት ደግሞ ከወላይታ ድቻ ይገናኛሉ።
ከአመሻሽ 12:00 ጀምሮ በተደረገው ጨዋታ ደግሞ ባሳለፍነው ሳምንት በወላይታ ድቻ የተረታው መሪው ኢትዮጵያ መድን 1 ለ 0 አሸንፏል።
በጨዋታው መሀመድ አበራ ከበረከት ካሌብ ከቀኝ መስመር አቅጣጫ የተሻገረለትን ኳስ በማስቆጠር ቡድኑን አሸናፊ አድርጓል።
መሐመድ ዛሬ ያስቆጠረውን ግብ ተከትሎ በውድድር ዓመቱ ያስቆጠራቸውን የግብ ብዛቶች 6 ማድረስ አስችሎታል።
መድን ማሸነፉን ተከትሎም ነጥቡን 38 በማድረስ ከተከታዩ ኢትዮጵያ ቡና ያለውን ልዩነት ወደ ስድስት አስፍቷል።
የአዳማ ቆይታው መልካም ያልሆነው ድሬዳዋ ከተማ በበኩሉ ከድል ጋር ከተራራቀ አስር ጨዋታዎች ተቆጥረዋል።
የይታገሱ እንዳለው ቡድን አዳማ ላይ ካደረጋቸው ዘጠኝ የሊጉ ጨዋታዎችም በአምስቱ ነጥብ ሲጋራ በአራቱ ተሸንፏል።
ቡድኑ ከደረጃ ሰንጠረዡ በሁለት ነጥቦች ብቻ ርቆ በ21 የነጥብ ብዛቶች 14ኛ ላይ ተቀምጧል።
በ22ኛ ሳምንት መርሐግብር ኢትዮጵያ መድን ኢትዮጵያ ንግድ ባንክን እንዲሁም ድሬዳዋ ከተማ ቅዱስ ጊዮርጊስን ይገጥማሉ።


