የኢትዮጵያ ሴቶች ብሔራዊ ቡድን የ2026 የአፍሪካ ዋንጫ አንደኛ ዙር የማጣሪያ የመልስ ጨዋታውን በነገው ዕለት ከዩጋንዳ አቻው ጋር ያደርጋል።
ባሳለፍነው አርብ በካምፓላ ሀምዝ ስታዲየም ላይ የ2 ለ 0 ሽንፈት ያስተናገደው ቡድኑ ቅዳሜ ምሽት ወደ ሀገሩ ከተመለሰ በኋላ ዛሬን ጨምሮ ባለፉት ሶስት ቀናት ልምምዱን አከናውኗል።
ነገ ከሚደረገው ወሳኝ ጨዋታ አስቀድሞም የብሔራዊ ቡድኑ ዋና አሰልጣኝ ዮሴፍ ገብረወልድ እና አምበሏ ሎዛ አበራ የቡድኑን ዝግጅት አስመልክቶ የቅድመ ጨዋታ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል።
በጨዋታው ላይ የነበረን እንቅስቃሴ የከፋ አልነበረም ያለው አሰልጣኝ ዮሴፍ ገብረወልድ በጨዋታው ወቅት የነበረው የአየር ሁኔታ እና የሜዳ ሁኔታ ከባድ ቢሆንባቸውም እስከ መጨረሻዎቹ ደቂቃዎች ድረስ በምንችለው መንገድ ጨዋታውን ተቆጣጥረነው ነበር ብሏል።
- ማሰታውቂያ -
የመጨረሻ ደቂቃዎች የትኩረት ማጣት ከተጫዋቾች ልምድ ማጣት ጋር ተደምሮ ሁለት ግቦችን እንዲያስተናግዱ እንደዳረጋቸውም ተናግሯል።
ቡድኑ በጨዋታው ይዞ ለመቅረብ ያቀደውን የጨዋታ መንገድ ያልጠበቅነው ነው ባለው የተጋጣሚ ቡድን እንቅስቃሴ ምክንያት ማድረግ አለመቻሉን ገልጿል። ለዚህም የዩጋንዳ ብሔራዊ ቡድን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድንን በሚገባ አውቆ ወደ ጨዋታ መምጣቱ ዋነኛ ምክንያት ነው ሲል ተናግሯል።
“ተጋጣሚያችን እኔ ከማውቀው በላይ ስለ እኛ ቡድን ብዙ መረጃ ነበራቸው። እኛ ስንሰራ የነበርናቸውን ነገሮች በሙሉ 100 ፐርሰንት ነው ሜዳ ላይ ሲተገብሩ የነበረው። በተለይም በጣም ነው ፕረስ ሲያደርጉን የነበረው።”
“ልምምዶቻችን በሙሉ ከኋላ መስርተን ለመውጣት ነበር ስንሰራ የነበረው ከኳስ ጋር አድርገን ስንሰራ የነበረው እና የመጀመሪያ ዕቅዳችን ተበላሽቶብናል።ከኋላ መስርተን እንዳንወጣ በጣም ተጭነውናል።”
የቡድኑ ዝግጅትም ሆነ በጨዋታው በሜዳ ላይ የነበሩት ተጫዋቾች ለጨዋታ መንገዱ የሚሆኑ የነበረ ቢሆንም የተጋጣሚያቸው ጫና ማድረግ በፈለጉት መንገድ ጨዋታውን ለማስኬድ ችግር ነበር ብሏል።
ቡድኑ በጨዋታው ከ16 በላይ ረጃጅም ኳሶችን የተጫወተ ሲሆን ከነዚህም መካከል ሁለቱ ብቻ ለቡድኑ ተጫዋቾች ደርሰዋል። ይህም ፈልገነው አይደለም ተገደን ያደረግነው ነገር ነው ሲል አሰልጣኝ ዮሴፍ አብራርተዋል።
ብሔራዊ ቡድኑ በጨዋታው ላይ በዩጋንዳ አቻው ብልጫ ተወስዶበታል በሚል ለቀረበላቸው ጥያቄ ትንሽ ስሜታዊነት የተስተዋለባቸው አሰልጣኝ ዮሴፍ ተጋጣሚያችን በልጠው አላሸነፉንም ሲል ተናግሯል።
“ይሄን ያህል የተጋገነ ብልጫ አይደለም ያየነው። ይሄን ያህል ብዙ የኳስ ቅብብል ያደረገ ቡድኑ አይደለም የዩጋንዳ ብሔራዊ ቡድን ፤ ምክንያቱም ሜዳው በጣም ትልቅ ስለነበረ ሜዳውን እየለጠጡት የመስመር ኳስ እና የሚቀነስ ኳስ ለማግባት ነው ሲሞክሩ የነበሩት። ይሄን ያህል የበለጡን ነገር አይታየኝም።”
“በእርግጥ ተጋጣሚያችን ሜዳው ነው። ብዙውን ነገር ስለሚያውቁት በኛ ሜዳ ላይ የተሻለ ነገር ለማድረግ ሞክረዋል። ግን በዛ ልክ ደግሞ እኛም ከሜዳችን ውጪ እንደመጫወታችን መጠን የምንችለውን ነገር ለማድረግ ሞክረናል።ልጆቹ ያላቸውን ነገር አድርገዋል ሜዳ ላይ ፤ ምንም የቀራቸው ነገር የለም።”
ከተጋጣሚያችን የተሻሉ የግብ ዕድሎችን ፈጥረናልም ያሉት አሰልጣኙ የሴናፍ ዋቁማን እና እሙሽ ዳንኤልን ኳሶችን አንድ ለአንድ ተገናኝተው ዕድሎችን መጠቀም አልቻሉም ብሏል። እኛ እድላችንን አልተጠቀምንም እነሱ ግን ያገኙትን ዕድል ተጠቅመው አሸንፈውናል ሲልም አክሏል።
ተጋጣሚያችን ከኛ የተለየ ምንም ነገር የለውም የሚለውም ከአሰልጣኝ ዮሴፍ ገብረወልድ አንደበት የተሰማ ነው።
“ተጋጣሚያችን በእርግጠኝነት ከኛ የተሻለ ምንም ነገር የለውም።ማለት የተሰጣቸው ግምት ያሏቸው በሌሎች ሀገራት የሚጫወቱ ተጫዋቾች ያን ከግምት ውስጥ ማስገባት ካልሆነ በስተቀር ምንም የተለየ ነገር የላቸውም። በእንቅስቃሴ ከኛ የተሻለ ነገር አላሳዩንም ሜዳ ላይ።”
ጨዋታው አላለቀም ያለው አሰልጣኝ ዮሴፍ በሜዳችን እና በደጋፊያችን ፊት ለተመልካች የሚሆን እንቅስቃሴ አድርገን በምንችለው መጠን አሸንፈን ወደ ቀጣይ ዙር ለማለፍ ሙሉ ዕምነት በራሳችን አለን እናደርገዋለንም ሲል በራስ መተማመን ተናግሯል።
የቡድኑ አምበል ሎዛ አበራ በበኩሏ በካምፓላው ጨዋታ የብሔራዊ መዝሙር ሲዘመር በተለየ ስሜት ውስጥ ስለነበረችበት ሁኔታ ለቀረበለት ጥያቄ ተከታዩን መልስ ሰጥታለች።
“ስለ ሀገር ስሜት ሁሉም ሰው ይገባዋል ብዬ አስባለሁ። እዛ ጋር ሀገርን ነው የምትወክለው ፤ የኢትዮጵያ ብሔራዊ መዝሙር ሲዘመር እንደዚህ አይነት ስሜት የማይሰማው ሰው የለም ብዬ አስባለሁ። ኢትዮጵያ ትልቅ ሀገር ናት። እኔ ደግሞ ኢትዮጵያን እንደምወክል ሳስብ ደግሞ ያ ስሜት ተሰምቶኛል።”
ይህ ስሜት የርሷ ብቻ ሳይሆን የሁሉም ተጫዋቾች ስሜት ነው ያለችው ሎዛ ኢትዮጵያን ወክዬ በተጫወትኩበት ሁሉም ጨዋታዎች ላይ እንደዚህ አይነት ስሜት እየተሰማኝ ነው የተጫወትኩት ብላለች።
ሎዛ አበራ አክላም ስለ ነገው ጨዋታም ስትናገር ጨዋታው አልቋል ማለት አይደለም በደጋፊያችን ፊት እና በሜዳችን እንደምናሸንፍ እርግጠኞች ነን ስትል ገልፃለች።
“የመጀመሪያውን ጨዋታ ተሸንፈን መጥተናል። ነገር ግን ጨዋታው አልቋል ማለት አይደለም። ነገ ሌላ 90 ደቂቃ አለን በዛ ዘጠና ደቂቃ አሸንፈን እንደምናልፍ በጣም እርግጠኞች ነን።የልጆቹም ስነ ልቦና ያለን ስሜት አሪፍ ነው።አሰልጣኛችንም ማድረግ ያለባትን እያደረገ ነው። ከእግዚአብሔር ጋር የተሻለ ውጤት አሰንደማንረን እና ወደ ቀጣዮ ዙር እንምናልፍ እምነቱ አለኝ።”
የኢትዮጵያ እና የኡጋንዳ ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ጨዋታ ነገ ከቀን 9:00 ጀምሮ በአበበ ቢቂላ ስታድየም ይደረጋል።


