የኢትዮጵያ ሴቶች ብሔራዊ ቡድን በ2026 የአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ የመጀመሪያ ጨዋታውን ከኡጋንዳ አቻው ጋር የፊታችን አርብ ከሜዳው ውጪ ያደርጋል።
ቡድኑ ላለፉት ሁለት ሳምንታት በጂም እና በሜዳ ላይ ዝግጅቱን ሲያደርግ የቆየ ሲሆን ከጅቡቲ ብሔራዊ ቡድን ጋርም ሁለት የአቋም መለኪያ ጨዋታዎችን በአበበ ቢቂላ ስታድየም አድርጓል።
ቡድኑ በነገው ዕለት ወደ ኡጋንዳ ካምፓላ ከተማ ከማቅናቱ በፊቴም በዛሬው ዕለት ዋና አሰልጣኙ ዮሴፍ ገብረወልድ ፣ የቡድኑ አምበል ታሪኳ በርገና እና የፌዴሬሽኑ ዋና ፀኃፊ አቶ ባህሩ ጥላሁን በተገኙበት ጋዜጣዊ መግለጫ ተሰጥቷል።
የአሰልጣኝ ዮሴፍ ገብረወልድን ውል ዝርዝር ሁኔታ በማብራራት መግለጫውን ያስጀመሩት የፌዴሬሽኑ ዋና ፀኃፊ አቶ ባህሩ ጥላሁን አሰልጣኙ በወርሀዊ የ80 ሺህ ብር ደመወዝ ለሁለት ዓመታት ቡድኑን ለማሰልጠን ውል ማሰራቸውን ገልፀዋል።
- ማሰታውቂያ -
በውሉ ላይም ቡድኑን ወደ አፍሪካ ዋንጫ መመለስ በአስገዳጅነት መቀመጡን የጠቀሱ ሲሆን ያ ባይሆንስ ተብሎ ለቀረበላቸው ጥያቄ ተከታዩን ምላሽ ሰጥተዋል።
“ውል ገብተናል ፤ የገባነውን ውል ላይ ደግሞ አስገዳጅ ነገር ይኖራል። ያንን ፌዴሬሽኑ ይፈፅማል። ለአፍሪካ ዋንጫ አናልፍም ብለን አናስብም። ስለምናልፍ የአስገዳጁ ነገር ችግር አይፈጥርብንም።”
አሰልጣኝ ዮሴፍ የአርባምንጭ ከተማን የሴቶች ቡድን በመምራት ይገኙ እንደነበር የሚታወስ ሲሆን በብሔራዊ ቡድን ኃላፊነት ከመሾማቸው በፊት ከክለቡ ጋር ንግግር መደረጉን አቶ ባህሩ ተናግረዋል።
አርባምንጭ ከተማም ለሀገር እስከሆነ ድረስ በሚል ፈቃደኝነታቸው በመግለፅ ውሉን መቅደዳቸውን ተናግረዋል።
“ከአርባምንጭ ከተማ ክለብ ጋር ሰፊ ውይይቶችን አድርገናል። አሰልጣኙ ክለብ ይዞ ብሔራዊ ቡድን እንዲያሰለጥን አይደለም የምንፈልገው ፤ ሙሉ ለሙሉ ትኩረቱን በኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ላይ አድርጎ እንዲሰራ እንፈልጋለን። ከዚህ አንፃር ደግሞ ውል አለው በምን መንገድ ውሉን አፍርሰን ብለን ወደዚህ መምጣት ይችላል በሚለው ላይ ከክለቡ ጋር ፕሮፌሽናል በሆነ መንገድ አውርተን ከነሱ በኩልም ጥሩ ምላሽ አግኝተን ፤ ለሀገር እስከሆነ ድረስ ችግር እንደሌለባቸው ገልፀው የምስጋና ደብዳቤም ፅፈንላቸው በዛው አግባብ አሰልጣኙ የብሔራዊ ቡድን አሰልጣኝ ሊሆን ችሏል።”
ስለ ቡድኑ ዝግጅት በተመለከተ አሰልጣኝ ዮሴፍ ገብረወልድ የሊጉን መቋረጥ እና የዝግጅት ጊዜ ማነስ ተፅዕኖ እንዳሳደረባቸው አልሸሸጉም። እንደ አሰልጣኙ ከሆነም የመጀመሪያውን ሳምንት በጂም እና በሜዳ ላይ ሲሰሩ ቆይተው በሁለተኛው ሳምንት ደግሞ በቀን አንድ ጊዜ በሜዳ ላይ ልምምዳቸውን ሲከውኑ ቆይተዋል።
ከጅቡቲ ብሔራዊ ቡድን ጋር የተደረጉት ጨዋታዎች ያን ያህል ሉሲዎቹን የፈተኑ ባይሆኑም ብዙም ይታይ ያልነበረውን ከሌላ ሀገር ጋር የወዳጅነት ጨዋታ ማድረጉን በበጎ ጎን ጠቅሰዋል።
የኡጋንዳ ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ጠንካራ መሆኑን ያነሱት አሰልጣኝ ዮሴፍ ቡድኑ ያደረጋቸውን ያለፉ የወዳጅነት ጨዋታ ቪዲዮዎች አግኝተው መመልከታቸውን ተናግረዋል።
“የኡጋንዳ ብሔራዊ ቡድን ጠንካራ እንደሆነ ይታወቃል። ከሀገር ውጪ የሚጫወቱ ተጫዋቾች እንዳሏቸው ይታወቃል። የወዳጅነት ጨዋታ እነሱ እንኳን ያደረጉት ከሁለት ወር በፊት ነው። ከሞሮኮ ፣ ከዲሞክራቲክ ኮንጎ እና ከአልጄሪያ ጋር ነው የተጫወቱት የነዛን የአቋም መለኪያ ጨዋታዎች ቪዲዮዎች አግኝተን ለማየት ሞክረናል። ምን ጠንካራ ምን ደካማ ጎን አላቸው የሚለውን ከዛ በመነሳት አንዳንድ ነገሮችን እየሰራን ነው ያለነው።”
የኡጋንዳ እና የኢትዮጵያ ሴቶች ብሔራዊ ቡድኖች በተደጋጋሚ ጊዜ በተለያዩ ውድድሮች ተገናኝተው ጨዋታ አድርገዋል።
በ2022 የአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ ላይም በመጀመሪያው ዙር ጨዋታ የኡጋንዳ ብሔራዊ ቡድን በመለያ ምት ማሸነፉ አይዘነጋም።
ከዚህም ጋር በተያያዘ አሰልጣኝ ዮሴፍ ገብረወልድ ምንም እንኳን ከዚህ ቀደም ከውድድሩ ውጪ ቢያደርጉንም ያ ማለት አሁንም ከውድድሩ ውጪ ያደርጉናል ማለት አይደለም ብለዋል።
የቡድኑ አምበል ግብ ጠባቂዋ ታሪኳ በርገና በበኩሏ በተደጋጋሚ ከኡጋንዳ ጋር መጫወታቸውን በመጥቀስ የማሸነፍ ብልጫውን ቢወስዱም በቀጣይ በምናደርገው ጨዋታ የነበረንን ክፍተተ አስተካክለን እንቀርባለን ብላለች።
“የምንገጥመው የኡጋንዳ ብሔራዊ ቡድንን ነው። የኡጋንዳ ብሔራዊ ቡድን ማለት ብዙ ጊዜያቶች በተለያዩ መድረኮች የተገናኘንበት አጋጣሚዎች አሉ። ብልጫውን ይወስዱታል የማሸነፍ ፤ በቀጣይ በምናደርጋቸው ጨዋታዎች ያን ነገር አስተካክለን ወደ ሜዳ እንቀርባለን። ምክንያቱም ሁሌ የሚያሸንፈንን ቡድን ማገናዘብ አለብን ብዬ አስባለሁ።”
“እንደ ግለሰብም እንደ ብሔራዊ ቡድን አምበልም ተደጋጋሚ ጊዜ ውጤት ይዘወብን ይሄዳሉ። በህብረት በሚሰሩት ነገር ነው ያንን ነገር የሚያደርጉት ፤ ለምሳሌ ብዙ ጋዜጠኞች በሜዳ ውስጥ ይኖራሉ። እነርሱ የሚሳሳቱትን ስህተት ለአሰልጣኞች ያቀርባሉ ያ ማለት ከአሰልጣኙ አጠገብ ይሆናሉ። ይህ በሚሆን ሰዓት እነርሱ የተሻለ ሆነው ይመጣሉ። በይበልጥ ስህተታቸው ላይ ስለሚሰሩ አንድ አሰልጣኝ ብቻ አይደለም የሚጠየቀው። በእግር ኳሱ ውስጥ ያሉ እያንዳንዱ የሚዲያ አካልም ሆነ አሰልጣኝ በህብረት ይሰራሉ እና ያ ነገር ደግሞ እኛ ጋርም ቢለመድ እና ብንሰራ ፤ ምክንያቱም ሚዲያው ላይ ያላቹ ስለሆናቹ ያን ነገር ብታዩ እና ድክመቶቻችን ላይ ትኩረት ብናደርግ የዚን ያህል ጊዜም አይፈጅብንም የአፍሪካ ዋንጫ ለመግባት።”
ታሪኳ በርገና አክላም ብሔራዊ ቡድኑ ያለ አሰልጣኝ መቆየቱ በተጫዋቾች ስለፈጠረው ስሜት ለቀረበላት ጥያቄ አስገራሚ መልስ ሰጥታለች።
“ተጠያቂ የምናደርገው ራሳችንን ነው። ለምሳሌ ይሄን የአፍሪካ ዋንጫ የምናጣ ከሆነ ብዙ የምናጣቸው ነገሮች አሉ። ተጠያቂ የምናደርገው ራሳችንን ስለሆነ ስለሆነ በቁጭት ውስጥ ነው የምንቀመጠው ፤ የተለየ ነገር ይፈጠራሉ ብለን የምናስባቸው ነገሮች የሉም። ነገር ግን ተጠያቂነት አሁን ላይ ላለው ነገር ትርፋማ ያደርገናል ብዬ አስባለሁ።”
“ደግሜ የምለው ተጠያቂ የምናደርገው እራሳችንን ነው። እንድንወጣም ወይንም ውድድሩን እንድንሳተፍ የሚያደርገን ያ ነገር ስለሆነ ቁጭቱን ወደራሳችን መውሰድ ጥሩ ነገር ነው ብዬ አስባለሁ።”
ዋና አሰልጣኙ ዮሴፍ ገብረወልድ ቀዳሚው ጨዋታ ከሜዳ ውጪ እንደመሆኑ መጠን ለጨዋታው የሚሆን ታክቲክ ይዘን እናቀርባለን በቻልነው መጠን ጨዋታውን እዛው ጨርሰን ለመምጣት እንጥራለን ፤ ጊዜው ቢያጥርም ለዚህ ጥሩ ዝግጀት አድርገናል ሲሉ ተናግረዋል።
አሰልጣኝ ዮሴፍ ገብረወልድ ሌላ የቀረበላቸው ጥያቄ በኡጋንዳ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ካምፓላ ኩዊንስን እየመራ ሊጉን እየመራ ከሚገኘው እና ከቡድኑ ስድስት ተጫዋቾች ለኡጋንዳ ብሔራዊ ቡድን ካስመረጠው አሰልጣኝ ፍሬው ኃይለገብርኤል ጋር ስለ ኡጋንዳ ብሔራዊ ቡድን መረጃዎችን ካገኙ የሚል ነበር።
አሰልጣኙ በቅድሚያ ጥያቄውን ቢያልፉትም በድጋሚ ተጠይቀው የኡጋንዳ ሊግም በመሀል ተቋርጦ አሰልጣኝ ፍሬው እዚህ እንደነበር በማንሳት እስካሁን ግን ስለ ኡጋንዳ ብሔራዊ ከቀድሞው የኢትዮጵያ ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝ ፍሬው ኃይለገብርኤል ጋር አለመነጋገራቸው ጠቅሰዋል።
አሰልጣኝ ዮሴፍ አክለውም ምንም እንኳን ቡድኑ ነገ ወደ ስፍራው አምርቶ በመጪው አርብ ጨዋታውን የሚያደርግ ቢሆንም ጊዜ ስላለን እዛ ከደረሰን በኋላ ከአሰልጣኝ ፍሬው ጋር እንነጋራለን ብለዋል።


