” የምወድቅ መስሏቸው ቢገፉኝም ሰቅለውኝ አርፈውታል “
” የ ሱዳኑን ጠንቋይም ቢሆን ይዛችሁ ግቡና አሸንፉ “
ወንድማገኝ ማርቆስ(ቾምቤ) /ጅማ አባጅፋር/”
በዘንድሮው የቤት ኪንግ ኢትዮጵያ ፕርሚየር ሊግ በጅማ አባ ጅፋር መልካም ጅማሮን ካሳዩ ተጫዋቾች መካከል አንዱ ነው ።
- ማሰታውቂያ -
ያለፉትን ሁለት አመታት በ ጅማ አባጅፋር በመጫወት ላይ የሚገኘው ወንድማገኝ ማርቆስ ምንም እንኳ ቡድኑ በተለያዩ የሜዳ እና ከሜዳ ውጪ አጣብቂኝ ውስጥ ቢገኝም የቡድኑ ቋሚ ተሰላፊ በመሆን ጥሩ ብቃቱን ሲያሳይ ቆይቷል ።
ወንድማገኝ ማርቆስ በክለቡ የተለያዩ ወቅታዊ ጉዳዮች ፣ ስለ ወደፊት እንዲሁም ስለ ራሱ የተለያዩ ሀሳቦችን ከሀትሪክ ስፖርት ፀሀፊ ቅዱስ ዮፍታሔ ጋር ቆይታን አድርጓል ።
ስላለፈው ውጣ ውረድ . . . . . . .
እዚህ ደረጃ ለመድረስ በጣም ከባድ ነገር ነው ያሳለፍኩት እንደዚህ እንደዚህ ብዬ ባላወራው ደስ ይለኛል ፣ የምወድቅ መስሏቸው ሲገፉኝ ሲገፉኝ ሰቅለውኝ አርፈውታል ። እኔ እዚህ ቦታ ለመድረሴ ጠንካራ እና ብርቱ ስለሆንኩኝ ነው ። የሆነ አባባል አለ ሁሌ አነባታለው መንፈስ ታድሳለች . . . ሁሌ ፈጣሪ ዛሬ የሚፈትነን ነገ ለሚመጣ ከባድ ችግር ራሳችንን እንድናዘጋጅ ነው ። አንዱን የህይወት ፈተና ባለፍክ ቁጥር አይበገሬ ማንነትህ ጎልቶ ይወጣል ፤ ስለዚህ ለምን ይሄ ችግር ገጠመኝ ብዬ አላማርርም ።
ስለ ጅማ የመጨረሻው ጨዋታ ተነሳሽነት . . . . . .
ብዙም የተለየ ምክንያት ያለው አይመስለኝም ፣ ግን የተለየው ነገር የመጨረሻ ጨዋታ መሆኑ ነው ። ከ ቡድን አጋሮቼ ጋር ያወራነው ይህን ጨዋታ አሸንፈን የመጨረሻ ጨዋታ እንደመሆኑ በቃ ደስ ብሎን እረፍቱን በደስታ እንጠቀመው ተባብለን ገባን ከዛህ ፈጣሪ ያለው ሆነ ።
የከተማው ከንቲባው መተው ያሉን ነገር ምንም የተለየ ነገር ያሉት ነገር የለም ግን በሰዓቱ ለእኛ ጊዜ ሰተው መምጣታቸው እራሱ በቂ ነበር ።
የተናገሩት ነገር ደስ ይላል ምንም ላስጨንቃቹ እና ላስገድዳቹ አይደለም የመጣሁት ብዙ ችግር እንዳለብን አውቃለው ። አንድ ሰው ደሞዝ ሳይከፈለው እንደዚህ መቆየታቹ እራሱ ጀግኖች ናችሁ ፣ ነገር ግን በቃ የተቻላችሁን አርጋችሁ ዉጡ ነበር ያሉን ።
እንደውም አንድ የሚያስቅ ነገር ነግረውን ነበር የወጡት ዛሬ የ ሱዳኑን ጠንቋይ ቢሆንም ይዛቹ ግቡና አሸንፋ ብለው አስቀውን ነበር በወቅቱ የተለያየነው።
በቀጣይ ወንድማገኝ . . . . . . .
እንደ ኳስ ተጫዋች የእኔ ግብ ጥሩ ቦታ መድረስ ነው እና አሁን ያለሁበት ቦታ እኔ ምፈልግበት ቦታ አይደለሁም ። ከ ፈጣሪ ጋር ከዚህ በላይ ጠንክሬ ሰርቼ ትልቅ ቦታ መድረስ የእኔ ትልቁ እምነት ነው።
ስለ ክለቡ ችግሮች እና የ ደሞዝ ሁኔታ. . . . . . .
ጅማ አባ ጅፋር ትልቅ ቡድን ነው ፣ ነገር ግን አሁን ላይ ያለው ነገር ግን ትልቅነቱን በሁሉም ሰው ውስጥ ጥያቄን የሚፈጥር ሆኗል ። ብዙ ችግሮች በክለባችን አሉ ነገር ግን ይህን ማውራት በእኔ አያምርም ባወራው ስለዚህ ቢቀርብኝ ይሻላል ።
አሁንም ላይ የ ደሞዝ ችግር አለ አልተቀረፈም ፣ እንደሁም በትላንትናው ዕለት ስብሰባ ነበረን ከ ክለቡ ስራ አስኪያጅ ጋር የስብሰባው አጀንዳ ስለ ደሞዝ ነበር ፣ ጥያቄውን አቀረብን የእነሱም ምላሽ በዚህ ሳምንት ይከፈላቸዋል የሚል ሀሳብ ሰተውን ተነጋግረን ለመለያየት ችለናል ። ያው እንግዲህ የስብሰባ መጨረሻው ጭብጨባ ነው ።
ስለ ሊጉ ጉዟቸው ፣ ደጋፊው እና በቀጣይ . . . . . .
ቡድናችን አጀማመሩ ጥሩ አልነበረም ፣
የ ዝግጅት ጊዜ አናሳ መሆኑ እና አንዳንድ ያልተሟሉ ጥቅማጥቅሞች ለውጤት ቀውስ ዳርጎናል። ሌላው ነገር ስለ ወራጅ ስለሚባለው ነገር አናስብም ግን እንደዚህ ከቀጥልን ስጋት ውስጥ መግባታችን አይቀሬ ነው ። አሁን ላይ ሁለት ጨዋታ ብናሸንፍ ደረጃችን ከፍ ይላል ከ እኛ በላይ ያሉት ብዙም አልራቁም ።
ስለዚህ ከዚህ በኃላ ባሉት ጨዋታዎች ነጥብ መያዝ አለብን ፣ አሁን ባለን ክፍተት ላይ ተጨዋቾች ለማምጣት የክለቡ ሀላፊዎች እየሰሩ እንደሆኑ ነግረውናል እውነት ከሆነ ይበረታታል ።
ደጋፊው ለክለቡ ሁሌም ጥሩ ነገር ነው ያለው ክለቡ ዉጤት ሲያገኝም ሲያጣም መጥተው ሌላ አገር ድረስ እንኳን ጊዜያቸውን ገንዘባቸውን ሰውተው ይደግፉናል ይበል የሚያስብል ነው።
በሊጉ አብሮት መጫወት የሚፈልገው . . . ..
እኔ በሊጉ አብሬው መጫወት የምፈልገው የፋሲል ከነማው ያሬድ ባዬ ጋር ነው ፣ በጣም ነው የማደንቀው እና የምወደው የመሀል ተከላካይ ተጫዋች ነው ።
ስለ ህልሙ . . . . . . . .
በእግር ኳስ ተጫዋችነት ያው ሁሉም እግር ኳስ ተጫዋች የሚያስበውን አስባለው ማንም ሰው ጥሩ ነገር ይፈልጋል እኔም ከእነዛ ሰዎች መሀል ነኝ ። በመጨረሻም የምለው አሁን ላለሁበት ቦታ ላደረሰኝ ለታላቁ ለእግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይሁን ሲቀጥል ለቤተሰቤ እና ለሁሉም ጓደኞቼ በጣም አመሰግናለው።