ኢትዮጵያ ከኤርትራና ከቡሩንዲ ጋር ተደለደለች-ከኤርትራ ጋርም የመክፈቻውን ጨዋታ ታደርጋለች
“የሴካፋን ዋንጫ እዚሁ ሀገራችን ላይ ለማስቀረት በሁሉም መልኩ ተዘጋጅተናል”
የዋልያዎቹ አጥቂ መስፍን ታፈሰ
በኢትዮጵያ አስተናጋጅነት የሚካሄደው እና ዕድሜያቸው ከ23 ዓመት በታች የሆናቸው ተጨዋቾች የሚሳተፉበት የምስራቅና መካከለኛው አፍሪካ /ሴካፋ/ ዋንጫ የእግር ኳስ ውድድር በሶስት ምድብ ዘጠኝ ሀገራትን ከፍሎ ከዛሬ ጀምሮ የሚካሄድ ሲሆን ሀገራችን ኢትዮጵያም በምድብ ሁለት ከኤርትራና ከቡሩንዲ ጋር ተደልድላ ጨዋታዋን የምታደርግ ሲሆን የመጀመሪያ የመክፈቻ ግጥሚያዋንም ከቀድሞ ድንበሯና ከአሁን ጎረቤቷ ከኤርትራ ብሔራዊ ቡድን ጋር ዛሬ በ10 ሰዓት የምታደርግ ይሆናል፡፡
- ማሰታውቂያ -
በባህርዳር ኢንተርናሽናል ስታድየም በሚጀመረው በዚህ ውድድር በሌላኛው ምድብ አንድ ኡጋንዳ፣ ታንዛኒያና ተጋባዧ ዲሞክራቲክ ሪፖብሊክ ኮንጎ ሲመደቡ ከዚሁ ምድብ ዛሬ በ8 ሰዓት ኡጋንዳ ከዲሞክራቲክ ሪፖብሊክ ኮንጎ የመክፈቻ ጨዋታዋን ታደርጋለች፤ በምድብ ሶስት ደግሞ ጅቡቲ፣ ደቡብ ሱዳንና ኬንያ ሊደለደሉ ችለዋል፡፡
ዋልያዎቹ ለዚሁ የሴካፋ ዋንጫ ውድድር ዝግጅታቸውን በአሰልጣኝ ውበቱ አባተና በረዳቶቹ አንዋር ያሲንና አስራት አባተ እንደዚሁም ደግሞ በግብ ጠባቂው አሰልጣኝ ደሳለኝ ገብረ ጊዮርጊስ በመመራት በጥሩ ሁኔታ ሲሰሩ የከረሙ ሲሆን እዚህ ውድድር ተሳትፎአቸውን በሚመለከትና ሌሎችንም ጥያቄዎች በማንሳት ከቡድኑ የአጥቂ ስፍራ ተጨዋች መስፍን ታፈሰ /ቹንኬ/ ጋር ጋዜጠኛ መሸሻ ወልዴ ቆይታን አድርጎ ምላሽን ሰጥቶታል፤ ተከታተሉት፡፡
ስለ ሴካፋ ዝግጅታቸው
“ጥሩ ልምምድን ነው በተለያዩ ሜዳዎች ላይ ስንሰራ የነበረው። አራት የአቋም መለኪያ ግጥሚያዎችንም አድርገን እንዴት መጫወት እንዳለብንም በመረዳት ወደ መቀናጀቱ መጥተናል”።
ስለያዙት የተጨዋቾች ስብስብ
“ምርጥና ጥሩ ስብስብን ነው የያዝነው። ወጣት ተጨዋቾችን የያዝን እንደመሆናችንም አንድ ታሪክን መስራት ያስችለናል”።
ስለ ዛሬው ከኤርትራ ጋር ስለሚያደርጉት ጨዋታ
“ይህቺ ሀገር ቀድማ የእኛ ድንበር ብትሆንም እንደ ውድድር ዛሬ ልንፋለማት ተዘጋጅተናል።ጨዋታውን የደርቢ ያህል ስለምንመለከተው እና የመጀመሪያን ግጥሚያም ማሸነፍ ወደ ተከታዩ ዙር ለማለፍ ጥቅሙ ከፍ ያለ ስለሆነ የጨዋታው ባለ ድል እኛ እንሆናለን”።

በሴካፋ የሚሳተፈው ቡድን አዳዲስ ወጣት ተጨዋቾችን ማብዛቱ
“ይሄ ማለት የውድድሩ አንዱ ዓላማ ቢሆንም በስኳዱ ለተያዝነው ተጨዋቾች ደግሞ በምናሳየው ብቃት ነገ ለዋናው ቡድን እንድንጠራ ግብዐት ይሆነናልና የወጣት ተጨዋቾች መብዛትን የወደድኩት ነው”።
ለብሄራዊ ቡድን ተመርጦ ስለመጫወት
“ሀገርን ወክሎ መጫወት ትርጉም አለው፤ ስሜቱ ከፍ ያለም ነው። ታሪክህም ነው። ይሄን ዕድል ለማግኘት በመቻሌ በጣም ደስ ብሎኛል”።
ስለ ሴካፋ ድላቸው
“ዓላማችን ዋንጫውን ማንሳት ነው፤ ይህንንም ድል እናሳካዋለን”።
በሴካፋው ጎሎችን ያስቆጥር እንደሆነ
“የተሟላ ዝግጅትን ቡድናችን ሰርቷል። አሰልጣኞቹም እኛን አምነው ጥሩ ነገርን እንድንሰራላቸው ጠርተውናል። ከዚህ በኋላ አሁን የሚጠበቀው የእኛ ስራ ነውና እኔም በዚህ የውድድር ተሳትፎዬ ላይ ሀገሬን ለድል የሚያበቁ ጎሎችን የማስቆጥር ይመስለኛል”።
ወደ ውጪ ወጥቶ ለመጫወት ስላገኘው ድል
“አዎን አሁንም እንደከዚህ ቀደሙ እድሉን አግኝቼ ነበር። ከቤላሩስ ክለብም ነበር የመጣልኝ፤ ያም ሆኖ ግን በዚህ ሰዓት ላይ እኔ ለሀገሬ ብሄራዊ ቡድን መጫወትን ቅድሚያ ስለሰጠሁት ይሄ ጥሪው ሲደርሰኝ አላስደሰተኝምና መሄዱን ትቼዋለሁኝ”።


