41ኛው የምስራቅና መካከለኛው አፍሪካ ሀገሮች ከ23 አመት በታች የሴካፋ ሻምፒዮና ዛሬ በባህርዳር ከተማ በይፋ ይጀመራል፡፡ አዘጋጅዋን ሀገር ኢትዮጵያን ጨምሮ ዘጠኝ ሀገራት በሶስት ምድብ ተከፍለው ለአንድ ዋንጫ የሚደርጉት ፍልሚያ ዛሬ በባህር ዳር ኢንተርናሽናል ስታዲየም በይፋ ሲጀመር የመክፈት ጨዋታቸውን አዘጋጅዋ ሀገር ኢትዮጵያን ከኤርትራ ጋር ያገናኛል፡፡
ቀደም ሲል የመክፈቻ ጨዋታውን ዩጋንዳና ዲ.ሪ.ኮንጎ እንደሚያደርጉ መርሃ ግብር የተያዘለት ቢሆንም የኮንጎ ከ23 አመት በታች ብ/ቡድን በተያዘለት ቀን ወደ አዲስ አበባ ባለመምጣቱ የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ ወደ እሁድ ለመገፋት ተገዷል፡፡
ለዚህ ጨዋታ ከሰኔ 4 ቀን ጀምሮ ዝግጅቱን በአዲስ አበባና በባህር ዳር ሲያደርግ የከረመው በአሰልጣኝ ውበቱ አባተ የሚመራው የኢትዮጵያ ከ23 አመት በታች ብ/ቡድን የውድድሩ ሻምፒዮን ለመሆን ከፍተኛ ዝግጅት ሲያደርግ የቆየ ሲሆን ከወዲሁም ለሻምፒዮናነት ከፍተኛ ግምት ተሰጥቶታል፡፡
የኢትዮጵያ ብ/ቡድንን በአምበልነት የሚመራው የያዝነው የውድድር አመት ከፍተኛ ጎል አግቢ፣ ኮከብ ተጨዋችና የቤትኪንግ ፕሪሚየር ሊግ ወጣት ተጨዋችነት ክብርን ደራርቦ የተጎናፀፈው የኢትዮጵያ ቡናው አቡበከር ናስር ይሆናል፡፡
- ማሰታውቂያ -
በሻምፒዮኑ ላይ የሚሳተፉት ሀገሮች ተጠናቀው እየገቡ ሲሆን ይሄ ዘገባ እስከተጠናከረበት ጊዜ ድረስ የዩጋንዳ፣ የኬንያ፣ የኤርትራና የቡሩንዲ፣ ባለፈው ሐሙስ ደግሞ የጅቡቲ ብ/ቡድኖች ውድድሩን ወደምታስተናግደው ባህር ዳር መግባታቸው ተረጋግጧል፡፡
ዛሬ በኢትዮጵያና በኤርትራ መካከል ከሚደረገው የመጀመሪያ ጨዋታ በፊት የመክፈቻ ሥነ-ስርዓት ይኖራል ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን ጨዋታዎች በሙሉ የቀጥታ ስርጭት ያገኛሉ? አያገኙም? የሚለው ጥያቄ እስከአሁን ይሄ ዘገባ እስከተጠናከረበት ሰዓት ድረስ ቁርጥ ያለ ምላሽን አላገኘም፡፡
የሻምፒዮናውን የቴሌቪዥን መብት የገዛው መቀመጫው ታንዛንቲያ የሆነው አዛም ቴቪ ቢሆንም እስከአሁን ወደ ባህርዳር ብቅ ብሎ ያደረገው ዝግጅት ካለመኖሩ አንፃር የመተላለፉ ነገር ላይ ጥያቄ እንዲነሳ እያደረገ ነው፡፡
የኢትዮጵያ ከ23 አመት በታች ብ/ቡድን የሚያደርጉትን ጨዋታ በክልሉ (አሚራ) ቴሌቪዥን የቀጥታ ስርጭት ሽፋን የመስጠት እንቅስቃሴ ቢኖርም የስርጭት መብቱ ባለቤት የሆነው የአዛም ቴቪ ፈቃድ የሚያስፈልግ በመሆኑ ፈቃድ ማግኘትና የኢትዮጵያ ብ/ቡድን ጨዋታዎች በአማራ ቲቪ የቀጥታ ሽፋን እንዲያገኙ ጥረት እየተደረገ መሆኑ ታውቋል፡፡ አለም አቀፍ ወረርሽኝ የሆነው ኮቪድ-19 ተከትሎ ውድድሩን የሚከታተሉ ተመልካቾች ቁጥርን በተመለከተ ገደብ የተቀመጠ ሲሆን የባህር ዳር ስታዲየም የኮቪድ-19 ፕሮቶኮልን በጠበቀ መልኩ ከ25 ሺህ በላይ ተመልካቾችን እንዳያስተናግድ ተወስኗል፡፡
ኢንተርናሽናል አርቢትር ዶ/ር ኃይለየሱስ ባዘዘው ከኢትዮጵያ በመሀል ዳኝነት ጨዋታውን እንዲመራ የተመረጠ ብቸኛው ዳኛ ሲሆን የቀድሞዎቹ ኢንተርናሽናል አርቢትሮች ልዑል ሰገድ በጋሻው፣ ኃይለ መላክ ተሠማና አቶ ሠለሞን ገ/ስላሴ በኮሚሽነርነትና በኮርድኔተርነት መመረጣቸው ታውቋል፡፡
ከ23 ዓመት በታች የሴካፋ ሻምፒዮና የምድብ ድልድል
. በምድብ አንድ ዲ.ኮንጎ፣ዩጋንዳና ታንዛኒያ
. በምድብ ሁለት ኢትዮጵያ፣ኤርትራና ብሩንዲ
. በምድብ ሶስት ደቡብ ሱዳን፣ኬንያና ጅቡቲ ሆነው ተደልድለዋል።
የሴካፋ ከ23 አመት በታች ሻምፒዮና የኢትዮጵያ ብ/ቡድን ጨዋታዎች
ቅዳሜ ሐምሌ 1߀
ኢትዮጵያ ከኤርትራ
ቅዳሜ ሐምሌ 17
ኢትዮጵያ ከቡርንዲ