“ለቅ/ጊዮርጊስ መጫወት ያለውን አደራና ሀላፊነት አውቄ ነው ፊርማዬን ያኖርኩት”
በረከት ወልዴ /ቅ/ጊዮርጊስ/
“ወደ ቅ/ጊዮርጊስ ሳመራ ምክንያት ኖሮኝና የሚጠበቅብኝንም ሀላፊነትና አደራ አውቄ ነው ፊርማዬን በክብር ያኖርኩት፤ ከዚህ ቡድን ጋርም ትልቅ ስኬትን የመጎናፀፍም እልም አለኝ” የሚል አስተያየቱን ለሀትሪክ ስፖርት ጋዜጣ አዘጋጅ ጋዜጠኛ መሸሻ ወልዴ /G.BOYS/ የሰጠው ተጨዋች በክረምቱ የተጨዋቾች ዝውውር መስኮት በወላይታ ድቻ የነበረውን የውል ጊዜ በማጠናቀቁ ከቀናት በፊት ለቅ/ጊዮርጊስ ለሁለት ዓመታት ለመጫወት ፊርማውን ያኖረው የአማካይ ስፍራው ተጨዋች በረከት ወልዴ ነው።
ለኢትዮጵያ ዕድሜያቸው ከ23 ዓመት በታች ለሆናቸው የብሄራዊ ቡድን በመመረጥ በሀገራችን አስተናጋጅነት ለሚካሄደው የምስራቅና መካከለኛው አፍሪካ /ሴካፋ/ ዋንጫ ለመመረጥ የቻለው እና በቤትኪንግ ፕሪምየር ሊጉ ላይም ለወላይታ ድቻ በመጫወት ተስፋ ሰጪ እንቅስቃሴን በውድድሩ ቆይታው ያሳየውና በአጨዋወት ባህሪውም ከቼልሲው ንጎሎ ካንቴ ጋር አመሳስለውት በእሱ ስም እየጠሩት ያለው በረከት ወልዴ ከሀትሪክ ስፖርት ጋዜጣ ጋር ከወላይታ ድቻ ጋር ተለያይቶ ወደ ቅ/ጊዮርጊስ ክለብ ስላደረገው ዝውውር፣ በአዲሱ ቡድኑ ስለሚጠብቀው ሁናቴ፣ በወላይታ ድቻ ስለነበረው ቆይታ፣ በአገራችን አስተናጋጅነት ስለሚካሄደው የሴካፋ ዋንጫና ስለሚያስመዘግቡት ውጤት እንደዚሁም ከራሱ ብቃት ጋር በተያያዘ አጠር ያሉ ጥያቄዎችን ለተጨዋቹ አቅርበንለት ምላሹን ሰጥቶናል። ቃለ-ምልልሱም እንደሚከተለው ቀርቧል፤ ተከታተሉት።
በወላይታ ድቻ የነበረውን የውል ዘመን አጠናቆ ለቅ/ጊዮርጊስ ክለብ ለመጫወት ፊርማውን ስለማኖሩ
- ማሰታውቂያ -
“ለቅ/ጊዮርጊስ መጫወትን ያለምኩት ገና ወደ ወላይታ ድቻ የዋናው ቡድን እንዳደግኩ ነው። ያኔ የእነሱን ቡድን በተቃራኒነት መግጠምም ከያዙት የተጨዋቾች ስብስብና ከክለቡ ትልቅነትም አንፃር የራስህን ብቃት ለማሳየት የምትጥርበት ሁኔታም ስላለ ለዚህ ቡድን መጫወትን የማይፈልግ አንድም ተጨዋች የለምምና ወደ ቡድኑ በመግባት ይሄን እልሜን ከአራት ዓመታት ቆይታ በኋላ በመጫወት ላሳካው ስለተዘጋጀውኝ በጣም ደስ ብሎኛል”።
ለቅ/ጊዮርጊስ ለመጫወት ፊርማህን ስታኖር ስለ ክለቡ ምን ምን ነገሮችን አውቀህ ነው የመጣከው?
“ወደዚህ ቡድን ዝም ብዬ ጓዜን ጠቅልዬ እንደማልመጣ አስቀድሜ ነው የወላይታ ዲቻ ተጨዋች በነበርኩበት ሰዓት ላይ የማውቀው። ቅ/ጊዮርጊስ ትልቅና በውጤታማነት የታጀበ ክለብ እንደሆነ ከእዛ ውጪም ለዚሁ ቡድን ስትጫወት ያለው አደራና ሀላፊነትም በጣም ከፍ ያለ እንደሆነም ገና ለዚህ ቡድን ለመጫወት ፍላጎትን ካሳደርኩበት ጊዜ ጀምሮም የተረዳሁት ነገር ስላለ በዚህ መልኩ ነው ወደ ክለቡ በመምጣት ፊርማዬን ማኖር የቻልኩት”።
በቅ/ጊዮርጊስ ቆይታው የተሳካ እና በውጤታማነት የታጀበ የጨዋታ ጊዜያቶችን ያሳልፍ እንደሆነ
“ወደ ቡድኑ ስመጣ ብዙ አደራና ሀላፊነት እንዳለብኝ ስለማውቅና ጠንካራ የሚባል ሰው ደግሞ በፈተና ውስጥ ሆኖም የሚያልፍ እንደሆነም ስለማስብ የዚህ ቡድን የተጨዋችነት ዘመን ቆይታዬ ስኬታማና ከውጤታማነት ጋር የተሳሰረ እንደሚሆንም እርግጠኛ ነኝ። ምክንያቱም ይሄ ቡድን አሁን ላይ ዋንጫ ካጣ አራተኛ ዓመቱን ይዟል። እኛ አዲስ ተጨዋቾች ወደዚህ ቡድን እንድንመጣ የተደረገውም ይሄን ቡድኑ የማይታወቅበትን ታሪክ ሽረን ቀድሞ ወደሚታወቅበት ሀያልነቱ እንድንመልሰውም ስለሆነ ለዛ ራሴን በጥሩ መልኩ አዘጋጅቼው በቡድኑ የተሳካ ጊዜን አሳልፋለው”።
ለወላይታ ድቻ የአራት ዓመታትን ቆይታ ካደረግክ በኋላ ነው ወደ አዲሱ ቡድንህ ቅ/ጊዮርጊስ ልታመራ የቻልከው፤ ጊዜያቶቹ ለአንተ ምርጥ ሆነው አልፈዋል?
” በጣም፤ ግልፅ የሆነና የታየ ነገር ነው እኮ። ከዓመት ዓመት በችሎታዬ ላይ ለውጦች እንዳሉኝ ምንም ጥርጥርም የለኝም። በተለይም ደግሞ ዘንድሮ በነበረው የቤትኪንግ ፕሪምየር ሊግ ሻምፒዮና ውድድር ላይ በጣም የተሳካ የውድድር ጊዜያትን ያሳለፍኩበትና በራሴም ላይ ከፍተኛ ለውጥንም የተመለከትኩበት እንደዚሁም ደግሞ ለብሄራዊ ቡድን ከመመረጥ ባሻገር ወደ ታላቁ ክለብ ቅ/ጊዮርጊስም ተፈልጌ የመጪው ዘመን ውድድር ላይ እንድጫወትም ፊርማዬን እንዳኖር የተደረግኩበትም ዓመት ስለነበር ያ ሊሆን
በመቻሉ ደስታዬ እጥፍ ድርብም ነው”።
ለወላይታ ድቻ የውድድር ዓመቱ በምን መልኩ እንዳለፈና ከክለቡ መለያየቱን በማስመልከት ስለሚለው ነገር
“ይሄ የውድድር ዓመት ለእኛ በሁለት መልኩ ያለፈ ነው። የመጀመሪያው በሜዳ ላይ እንቅስቃሴያችን ጥሩ ሆነን ሳለ በውጤት ቀውስ ውስጥ የቆየንበት ጊዜ ሲሆን ሌላው ደግሞ ከግማሽ ሲዝን በኋላ በአዲሱ አሰልጣኛችን አማካኝነት ወደ ውጤታማነቱም በማምራት የተጓዝንበት ሁኔታም ነበርና ያን ልመለከት ችያለሁ።
በወላይታ ድቻ የነበረኝን ቆይታ አጠናቅቄ ወደ አዲሱ ቡድኔ ስላመራሁበት ሁኔታ ደግሞ ማለት የምፈልገው ይህ ቡድን እኔን ከስር ኮትኩቶ በማሳደግ ለእዚህ እውቅናና ክብር ያበቃኝ ነው። የዚሁ ቡድን ተጨዋች ሆኜም ነው ለብሄራዊ ቡድንም ልመረጥ የቻልኩቴና ይሄን ባለውለታዬን ክለብ መቼም ሳልረሳው ላመሰግነው እፈልጋለሁ”።
ለኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ተመርጦ ለሴካፋ ዋንጫው እያደረጉ ስላሉት ልምምድ
“በጣም ጥሩ የሆነና ደስ የሚል ልምምድን በአሰልጣኛችን ውበቱ አባተ አማካኝነት እየተሰጠን ለውድድሩ በመዘጋጀት ላይ ነን። በአካል ብቃቱም በስነ-ልቦናውም ዝግጁም ነን። አብዛኛው ልምምድም ከኳስ ጋር በተያያዘ መልኩ በምን ጊዜ ኳስ መያዝና መጫወት እንዳለብንና በምን ጊዜ ደግሞ ኳሱን እየለቀቅን ወደፊት ማጥቃት ላይ ያተኮረን እንቅስቃሴ መጠቀም እንዳለብንም እየሰራንበት ስለሆነ በእስካሁን ልምምዳችን በጣም ደስተኛ ነን። በጨዋታ ዘመኔ እንዲህ ያሉ ልምምዶች ሁሌም ቢሆን ደስ የሚሉኝና የምመርጣቸው ናቸው፤ ለአገራችን የእግር ኳስ እድገትም የሚያዋጣው ይህ አጨዋወትም ይመስለኛልና ሁሌም ብንጠቀመው በጣም ነው ደስ የሚለኝ”።
ስለ ብሄራዊ ቡድኑ /u-23/ የተጨዋቾች ስብስብ
“ምርጥና ጥሩ አቅም ያላቸው ወጣት ተጨዋቾች ናቸው በአብዛኛው በስኳዱ ውስጥ ተመርጠው የተሰባሰቡት። ለዋናው የብሄራዊ ቡድንም ግብዐት የሚሆኑ ልጆችም በዚሁ ስብስብ ላይ እንደተካተቱና እነዚህ ተጨዋቾችም ጥሩ አቅም እንዳላቸውም አሰልጣኞቹ ከእኛ በላይ ጠንቅቀውም ያውቃሉና በሁላችንም ተጨዋቾች ብቃት ተስፋ ሰጪ ነገርን እየተመለከቱም ነው”።
ለሴካፋው ውድድር ለብሄራዊ ቡድን ስለመመረጡ
” ከዚህ በፊትም ገልጬዋለው የመመረጡን ዕድል አግኝቼ በክለቤ በኩል ሳይነገረኝ ቀርቶ ይሄን ዕድል ወደ ሽረ ለጨዋታ በተጓዝንበት ወቅት አውቄ በእኔ ፋንታ ሌላ ተጨዋች ተመርጦ ይህን ዕድል አጥቼ ነበር፤ በወቅቱ ብዙም አልተከፋሁም። አሁን ይህን የመመረጥ እድል አግኝቼ ውዲቷን ሀገሬን ላገለግላትና ለስኬታማነትም ላበቃት የተዘጋጀውበት ሰዓት ላይ ስለምገኝ በጣም ደስተኛ ነኝ”።
ለብሄራዊ ቡድን ተመርጦ መጫወት ስለሚኖረው ስሜትና በሴካፋው ውድድር ላይ ሊያመጡ ስላሰቡት ውጤት
“የሀገርን ባንዲራ በወከለ መልኩ መለያውን ለብሶ መጫወት መቻል ስሜቱ በጣም ደስ ይላል። ስትጫወት ብዙ ነገርንም ትማርበታለህ። እውቀትንም ትገበይበታለህ። ይህን ካልኩ ዘንዳ በሴካፋው ውድድር እኛ ኢትዮጵያኖች በውድድሩ ላይ ልናስመዘግብ ያሰብነው ውጤት አዘጋጅ ሀገር እንደመሆናችንም ዋንጫውን እዚሁ ለማስቀረት ነው። ይሄን ድል የሚያሳካ ምርጥ አቅምም አለን”።
በሴካፋ የመጀመሪያ የመክፈቻ ጨዋታን ከቀድሞ ድንበራችንና ከአሁኗ ጎረቤታችን ኤርትራ ጋር ስለማድረጋቸውና ስለሚያስመዘግቡት ውጤት
” ከኤርትራ ጋር የሚኖረን ጨዋታ ለእኛ የተለየ አይደለም። ሁሉም ተሳታፊ ሀገራት ለእኛ አንድ ናቸውና ከማንም ሀገር ጋር እንደምናደርገው ግጥሚያም ነው ጨዋታውን የምንመለከተው። ይሄም ጨዋታ ከዛም ውጪ ከምድባችን አንደኛ ሆነን ወደ ቀጣዩ ዙር ለማለፍም የጥርጊያ መንገዱን የሚያመቻችልንም ስለሆነ ከረጅም ዓመታት ቆይታ በዋላ ወደ አገራችን በመምጣት ሊጫወቱ ከተዘጋጁት የኤርትራ ወንድምቻችን ተጨዋቾች ጋር ደስ እያለን ጨዋታውን በማድረግ እነሱን አሸንፈናቸው ከሜዳ እንወጣለን”።
በእግር ኳስ ተጨዋችነት ዘመን ቆይታው ስለ ቀጣይ ጊዜ ራዕዩ
“ብዙ ጊዜ ራዕይ የሚገደብ ነገር አይደለም፤ ሁሌም የተሻሉ ነገሮች እንዲገጥሙህ ታቅዳለህና አሁን ላይ ከማስባቸው ነገሮች ውስጥ ወደፊት ጥሩ ነገርን ሰርቼ በፕሮፌሽናል ተጨዋችነት ደረጃ ወደ ውጪ ወጥቶ መጫወት ዋናው ምኞቴ ነው። ይሄን እንደማሳካውም እርግጠኛም ነኝ”።
ስናጠቃልል
“በእግር ኳስ ተጨዋችነት አሁን ለመጣሁበት መንገድ በቅድሚያ ፈጣሪ ሁሌም ይመስገንልኝና በሀሳብና እኔን በማሰልጠኑ ረገድም የብዙ ሰዎች እጅ አለበትና እነሱንና ቤተሰቦቼን ጭምር ለማመስገን እፈልጋለው። በኳሱም ለታላቅ ደረጃ ከመብቃት ባሻገር በአዲሱ ክለቤ ውስጥም ደማቅ የስኬት ታሪክን ማስመዝገብ እፈልጋለው”።