የኢትዮጵያ ቡና ስፖርት ክለብ በትናንትናው ዕለት በተደረገው እና ኢትዮጵያ መድን ሲዳማ ቡናን 3 ለ 0 በረታበት ጨዋታ ዙሪያ ለሊግ አክስዮን ማህበሩ በደብዳቤ ቅሬታ አቅርቧል።
ክለቡ በደብዳቤው ላይ ሊጉ ወደ አጓጊ የፉክክር ደረጃ ደርሷል በማለት በትናንትናው ጨዋታ ግን ከእግር ኳስ ስነ ምግባር ያፈነገጠ ተግባር ተፈፅሟል ብለን እናምናለን ብሏል።
“ግንቦት 20 ቀን 2017 ዓ.ም በ32ኛ ሳምንት የጨዋታ መርሀ ግብር በኢትዮጵያ መድን እና ሲዳማ ቡና መካከል የተደረገው ጨዋታ በዋንጫ ፉክክሩ ላይ ትልቅ ተፅእኖ የሚያሳድር ከእግር ኳስ ስነ ምግባር እጅግ የራቀ ተግባር ተፈፅሟል ብለን እናምናለን፡፡”

- ማሰታውቂያ -
ጨዋታው ለኢትዮጵያ የእግር ኳስ ዕድገት ማነቆ የሆነ ተግባራት መኖራቸውን የሚያሳይ ድርጊት መሆኑን የሊጉ አስተዳደሪ አካል ሊገነዘበው ይገባልም ሲል ገልጿል።
ስለዚህም የሊግ አክስዮን ማህበሩ የጨዋታውን ሂደት እንደገና ተመልክቶ እና አጣርቶ ለእግር ኳስ ቤተሰቡ እንዲያሳውቅ ፣ በተጨማሪም የእግር ኳስ ህጉ የሚፈቅደውን ተግባራዊ ያድርግ ሲል አመልክቷል።
በተጨማሪም ይህን ዓይነት ተግባር በፅኑ አወግዛለሁ ያለው ኢትዮጵያ ቡና መሰል ተግባራት ወደፊትም እንዳይደገሙ የፕሪሚየር ሊጉ አወዳዳሪ አካል በቶሎ ምላሽ እንዲሰጥበት ባስገባው የቅሬታ ደብዳቤ ጠይቋል፡፡



