የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የውድድር አመራር እና ስነ ስርዓት ኮሚቴ የ31ኛ ሳምንት የዲሲፕሊን ውሳኔዎችን ይፋ አድርጓል።
ትናንት ምሽት በተደረገው የሀዋሳ ከተማ እና የፋሲል ከነማ ጨዋታ መገባደጃ ላይ በቀይ ካርድ ከሜዳ የተሰናበቱት ሀብታሙ ተከስተ እና እስራኤል እሸቱ እያንዳንዳቸው የአራት ጨዋታዎች እግድ ተላልፎባቸዋል።
በተጨማሪም እያንዳንዳቸው የሶስት ሺህ ብር ቅጣትም ተወስኖባቸዋል።
የውድድር ዓመቱን አስረኛ የቢጫ ካርድ የተመለከቱቴ የቅዱስ ጊዮርጊሱ አጥቂ አማኑኤል ኤርቦ እና የወላይታ ድቻው ካርሎስ ዳምጠው ደግሞ እያንዳንዳቸው የሁለት ጨዋታዎች ዕግድ ተላልፎባቸዋል።
- ማሰታውቂያ -
በተጨማሪም ስንታየሁ መንግስቱ(አዳማ ከተማ) ፣ ጊት ጋትኩት(ሲዳማ ቡና) ፣ ያሬድ ዳርዛ(ወላይታ ድቻ) እና ኪሩቤል ኃይሉ(መቀሌ 70 እንደርታ) ደግሞ በአምስተኛ የቢጫ ካርድ ምክንያት እያንዳንዳቸው ከ32ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ታግደዋል።
በክለብ ደረጃ ወላይታ ድቻ እና ሀዋሳ ከተማ በሳምንቱ ጨዋታዎች በርካታ ተጫዋቾች የቢጫ ካርድ በመመልከታቸው እና ቅዱስ ጊዮርጊስ ደግሞ በቅድመ ስብሰባ ላይ ተወካይ ባለመገኘቱ እያንዳንዳቸው አምስት ሺህ ብር ተቀጥተዋል።


